ተመድ የቀድሞ አንድነት ፓርቲ አመራር አቶ አንዷለም አራጌ እንዲፈታ ጠየቀ


የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የቀድሞ አንድነት ፓርቲ አመራር የነበረው አቶ አንዷለም አራጌ እንዲፈታ ጠየቀ፡፡ የኢትዮጵያ መንግስት አቶ አንዷለምን ያሰረው ዓለም ዓቀፍ ድንጋጌዎችን በመጣስ እንደሆነ የገለጸው ተመድ፣ በመሆኑም መንግስት ፖለቲከኛውን ያለ ምንም ቅድመ ሁኔታ እንዲፈታ አሳስቧል፡፡ ድርጅቱ ባወጣው መግለጫ ላይ እንደገለጸው ከሆነ፣ አቶ አንዷለም አራጌ ለእስር የተዳረገው ያለ ምንም ጥፋት እና በደል ነው፡፡

በተባበሩት መንግስታት ድርጅት ውስጥ የእስረኞችን ጉዳይ የሚከታተለው ቡድን ባወጣው መግለጫ ላይ፣ የኢትዮጵያ መንግስት የጸረ ሽብር አዋጁን በመጠቀም ህጋዊ የፖለቲካ ሰዎችን እያጠቃ እንደሚገኝ ገልጿል፡፡ መግለጫው ይቀጥልና፣ አቶ አንዷለም አራጌ ለእስር የተዳረገውም የጸረ ሽብር ህጉን በመቃወሙ እንደሆነም ያትታል፡፡ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት፣ አቶ አንዷለም አራጌ ብቻ ሳይሆን ባልንጀሮቹ ጭምር ከእስር እንዲፈቱ የኢትዮጵያ መንግስትን አሳስቧል፡፡

በኢትዮጵያ የሚገኘው ስርዓት እጅግ አስከፊ መሆኑ በተለያየ ወቅት ሲገለጽ ቆይቷል፡፡ ይህን ጉዳይ የሀገሬው ህዝብ ብቻ ሳይሆን ዓለም ዓቀፍ ተቋማት እና መንግስታት ጭምር እየመሰከሩት ያለው ሐቅ ከሆነም ሰነባብቷል፡፡ በሕወሓት የሚመራው ይኸው ስርዓት፣ ለስልጣኑ የሚያሰጉትን ፖለቲከኞች ሁሉ እስር ቤት አስገብቷል፡፡ ከአንጋፋ ፖለቲከኞች ጀምሮ ገና ወጣት የሆኑ ፖለቲከኞችን እስር ቤት በማስገባት እየተበቀላቸው የሚገኘው አገዛዙ፣ ሰብስቦ ባሰራቸው ፖለቲከኞች፣ ጋዜጠኞች እና የሰብዓዊ መብት ታጋዮች የተነሳ ከዓለም ዓቀፍ የመብት ተከራካሪዎች ከፍተኛ ውግዘት እየገጠመው ይገኛል፡፡

BBN News 10/4/17

Leave a comment