ኢህአዴግ 98 ቢሊዮን ብር ነጠፈበት!! – “ታላቅ ሥራ ተሰርቷል! እናመሰግናለን!” ኦባንግ

ኢህአዴግ በዓለም ባንክ በኩል ከእንግሊዝ የዓለምአቀፍ ልማት ተራድዖ መ/ቤት ሊለግስለት ታቅዶ የነበረው 4.9 ቢሊዮን ዶላር (98ቢሊዮን ብር) የገንዘብ ድጋፍ ነጠፈበት፡፡ አቶ ሬድዋን አልነጠፈብንም ይላሉ፡፡ ኦባንግ ሜቶ በበኩላቸው “የታላቅ ሥራ ውጤት ነው፤ እናመሰግናለን” ብለዋል፡፡

8eba040e-8509-499d-b3a6-68e10e3a0bf6-1020x612_optጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ ጥቅምት 2፤2005 (OCTOBER 12, 2012) “ኢህአዴግ በ600 ሚሊዮን ዶላር አጣብቂኝ ውስጥ ገባ!! ብያኔው ከጸና ኪሣራው በቢሊዮን ዶላር ሊደርስም ይችላል!” በሚል ርዕስ የዓለም ባንክ በኢትዮጵያ ያካሂድ ስለነበረው ፕሮግራም በዘገበበት ወቅት የሚከተለውን ዜና አትሞ ነበር፡- “ከ1998ዓም ጀምሮ የመሠረታዊ አገልግሎት ጥበቃ ፕሮግራም (Protection of Basic Services “PBS Program”) በሚል በአራት ተከታታይና ሁለት ተጨማሪ የገንዘብ ድጎማ የሚደረግባቸውን ፕሮግራሞች የዓለም ባንክ በኢትዮጵያ ሲያካሂድ ቆይቷል፡፡ ይህ መሠረታዊ የሆኑ አገልግሎቶችን ለማሟላት ተወጥኖ የሚካሄድ ፕሮጀክት በትምህርት፣ በጤና፣ በእርሻ፣ በንጹህ ውሃ አቅርቦት፣ በገጠር መንገድ ሥራ፣ ወዘተ መስኮች ላይ እንዲውል (PBS I, PBS I-AF (Additional Financing), PBS II, PBS 11-AF, PBS-Social ACCOUNTABILITY Program and PBS III) በማለት በተለያዩ ደረጃዎች ለተከፋፈለው ኦፐሬሽን ማስፈጸሚያ የሚውለው ገንዘብ ከ13ቢሊዮን ዶላር የሚበልጥ ነው፡፡ ከዚህ ውስጥ ከፍተኛው የዓለም ባንክ ድርሻ 2ቢሊዮን ዶላር ሲሆን የተቀረው በሌሎች ለጋሽ መንግሥታት እና ድርጅቶች የሚሸፈን ነው፡፡ PBS III የተሰኘውን በሦስት ንዑሳን ፕሮግራሞች የተከፋፈለውን ፕሮጀክት ለማስፈጸም በአጠቃላይ የሚፈጀው 6.3ቢሊዮን ዶላር በላይ ነው፡፡”

ይህ ለመሠረታዊ ልማት እንዲውል በዓለም ባንክ በኩል የሚሰጠውን ገንዘብ የሚደጉሙት ምዕራባውያን አገራት ሲሆኑ አንዷ ተጠቃሽ አገር እንግሊዝ ናት፡፡ ሆኖም ኢህአዴግ ከምዕራባውያን በዓለም ባንክ በኩል የሚያገኘውን ገንዘብ ለራሱ የፖለቲካ መጠቀሚያነት እያዋለው መሆኑ ለዓለም ባንክ ተደጋጋሚ መረጃዎች ሲቀርቡ ቆይተዋል፡፡ በተለይ ሟቹ መለስ በቀጥታ በሰጡት ትዕዛዝ 424 የአኙዋክ ተወላጆች ከተገደሉ በኋላ ኢህአዴግ በቦታው ያሰማራው የመከላከያ ሠራዊት በሥፍራው የሚኖሩትን ከመኖሪያ ቀያቸው በማፈናቀል እምቢ ያሉትን በግድ በማስነሳት፣ በመግደል፣ አስገድዶ በመድፈር፣ በማሰቃየት፣ ወዘተ ግፍ ሲፈጽም መቆየቱ በተለያዩ ዓለምአቀፋዊ ዕውቅና ባገኙ ዘገባዎች ሲነገር ቆይቷል፡፡ የዓለም ባንክ ለመሠረታዊ ልማት በማለት የሚሰጠው ገንዘብ ኢህአዴግ ወታደሮቹን የግፍ ሥራ ላይ በማሰማራት ደመወዝ የሚከፍልበት መሆኑን በመጥቀስ ወደ ኬኒያ የተሰደዱ የክልሉ ነዋሪዎች አቤቱታ አቅርበው እንደነበር ጎልጉል በወቅቱ የዘገበው ዜና ነበር፡፡ ““ኢህአዴግ አንገቱን ታንቋል”፤ዓለም ባንክ ርምጃ ለመውሰድ ጫፍ ደርሷል” በሚል ርዕስ የተጻፈውን ዜና ለማንበት እዚህ ላይ ይጫኑ፡፡

ከዚሁ ጋር በተያያዘ “ሚስተር ኦ” በመባል የሚጠሩት አኙዋክ ተወላጅ ኢህአዴግ የዕርዳታ ገንዘብ ለሰብዓዊ መብት ረገጣና ለራሱ የፖለቲካ መጠቀሚያነት እንዳዋለው በመጥቀስ የእንግሊዝ መንግሥት ከግብር ከፋይ ዜጎቹ የሚያገኘውን ገንዘብ አምባገነንነት እየደገፈበት መሆኑን በተለይም የዓለምአቀፍ ልማት ተራድዖ መ/ቤቱ ተጠያቂ ስለሆነ ከዚህ እንዲታቀብ ክስ መመሥረታቸውይታወቃል፡፡ የክሱ ሒደት እየተካሄደ ባለበት ባሁኑ ወቅት ሚስተር ኦ በተደጋሚ እንደመሰከሩት ኢህአዴግ ነዋሪዎችን በግዳጅ ከቀያቸው በማፈናቀል የሚያካሂደው የግዳጅ ሰፈራና የመንደር ምሥረታ ሕገወጥ መሆኑ በመቃወማቸው በተደጋጋሚ ከፍተኛ ድብደባ እንደረሰባቸው ተናግረዋል፡፡ ብዙዎች ለአካላዊ ሥቃይ ደርሶባቸዋል፣ ሴቶች ክብረንጽህናቸው ተደፍሯል፣ አዛውንትና ህጻናት ለአሰቃቂ መከራ ተዳርገዋል፤ ይህንንም እርሳቸው እንዳዩ ሚስተር ኦ ይመሰክራሉ፡፡

የሚስተር ኦ የፍርድቤት ጉዳይ ወደ ውሳኔ ሊደርስ ባለበት ወቅት የልማት መ/ቤቱ ይህንን ዓይነት ውሳኔ መውሰዱ ከፍርድ ቤቱ ጉዳይ ጋር የሚያያዝ እንደሆነ ጉዳዩን በቅርበት የሚከታተሉ ይናገራሉ፡፡ የልማት ተራድዖ መ/ቤቱ ቃል አቀባይ ግን የመ/ቤታቸው ውሳኔ ከሚስተር ኦ የፍርድቤት ጉዳይ ጋር ያልተያያዘ እንደሆነ መናገራቸውን የእንግሊዙ ዘጋርዲያን ጋዜጣ ዘግቧል፡፡ መ/ቤቱ ለዚህ ውሳኔ የደረሰው ኢትዮጵያ “የዕድገት ስኬት” እያስመዘገበች በመምጣቷ የመሠረታዊ ልማት አገልግሎት የገንዘብ ዕርዳታ የማያስፈልጋት በመሆኑ ነው ብለዋል፡፡

ይህ መጠኑ እጅግ ከፍተኛ የተባለውና ለኢህአዴግ ንጹህ የውጭ ምንዛሪ ምንጭ የሚያስገኝ ገንዘብ እንደነጠፈበት መሰማቱን አስመልክቶ ጋዜጣው የኢህአዴግ ፅ/ቤት ሃላፊ የሆኑትን ሬድዋን ሁሴን በጠየቃቸው ወቅት የመለሱት አልነጠፈብንም የሚል እንድምታ ያለው ነው፡፡ “እነርሱ ያሉት ዕርዳታውን አንሰጥም ወይም እናቆማለን ሳይሆን ዕርዳታ አሰጣጡ እንደገና ይዋቀራል ነው” በማለት ሬድዋን ቃላቸውን ሰጥተዋል፡፡ ሆኖም 4.9 ቢሊዮን ዶላር (98ቢሊዮን ብር) ዕርዳታ ለመስጠት ከዓለምባንክ ጋር ስምምነት የነበረው የእንግሊዝ የልማት ተራድዖ መ/ቤት “ኢትዮጵያ አድጋለች” በማለት በ2015/2016 በፓውንድ 256ሚሊዮን ብቻ (5በመቶ) ዕርዳታ ለመስጠት መወሰኑን የኢህአዴግ ጽ/ቤት ሃላፊው ሬድዋን ሁሴን አላብራሩም፡፡

ኢህአዴግ ለዕርዳታ የሚሰጠውን ገንዘብ ዜጎችን ለማሰቃየት፣ ወታደር ለመቀለብ፣ ወዘተ እንደሚጠቀምበት በተደጋጋሚ ዘገባዎች እና ማስረጃዎች ሲወጡበት የከረመ ቢሆንም ማስረጃዎቹን ተከትሎ የዓለም ባንክ በዕርዳታ አሠጣጡ ላይ አንዳች ውሳኔ እንዳያደርግ ብዙሲደክም ቆይቷል፡፡ በዚህም ምክንያት ጉዳዩ ውሳኔ ሳይሰጥበት እንዲስተጓጎል በማድረግ ለሁለት ዓመታት ያህል እንዲጓተት ማድረጉን ከጉዳዩ ጋር ቅርበት ያላቸው ወገኖች ይመሰክራሉ፡፡

ለአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ (አኢጋን) ዋና ዳይሬክተር የሆኑት ኦባንግ ሜቶ ጉዳዩን ገና ከጅምሩ የሚያውቁትና ድርጅታቸው ለዓመታት ሲሰራበት የነበረ እንደሆነ ይናገራሉ፡፡ በመሆኑንም ይህንን የእንግሊዝ የልማት ተራድዖ መ/ቤት ውሳኔ የጋራ ንቅናቄያቸው ከደጋፊዎቹ ጋር በመሆን ያገኘው ድል እንደሆነ በፌስቡክ ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት አስታውቀዋል፡፡ “ገና ከጅምሩ ከጋራ ንቅናቄያችን ጋር በመሆን ይህንን ሥራ በመደገፍ የተባበራችሁንን ሁሉ እንኳን ደስ አላችሁ ለማለት እወዳለሁ፤ ታላቅ ሥራ ተሰርቷል፤ እናመሰግናለን” ብለዋል “ጥቁሩ ሰው” ኦባንግ ሜቶ፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘ አቶ ኦባንግ በተለይ ከጎልጉል ለቀረበላቸው አጭር ጥያቄ በሰጡት አስተያየት የጋራ ንቅናቄያቸው ደስታውን የገለጸው የልማት ገንዘብ በመቋረጡ ሳይሆን በልማት ስም የሚሰጠው ዕርዳታ ለሰብዓዊ መብት ረገጣ በመዋሉና ለዚህም ደግሞ ከበቂ በላይ ማስረጃ ድርጅታቸው ያለው በመሆኑ ነው፡፡ “አገር ብትለማ የሁሉም ደስታ ነው” ያሉት ኦባንግ አገርን በማልማት ሽፋን ደጋፊና ተቆርቋሪ የሌላቸውን ንጹሃን መበደልና የመኖር መብታቸውን መንፈግ ግን በየትኛውም መልኩ እርሳቸውም ሆነ አኢጋን የሚቀበለው እንዳልሆነ ተናግረዋል፡፡

ኢህአዴግ በቅርቡ አካሂዳለው ለሚለው ምርጫ እንደ ዕቁብ ዕጣ በማውጣትና በማስወጣት “አልደረሳችሁም” እያለ የተቀናቃኝ ፓርቲ አመራሮችን ከምርጫ እያስወገደ ባለበት፤ ሌሎችንም ሕጋዊ አይደላችሁም እያለ በተለጣፊ ድርጅት በማስበት ኅልውናቸውን እያሳጣ ባለበት ባሁኑ ወቅት በዜጎቹ ላይ የሚያካሂደውን መረን የለቀቀ የመብት ገፈፋ ለሥልጣን ያበቁትን ምዕራባውያንን ያስደሰተ እንዳልሆነ ይነገራል፡፡ የአውሮጳ ኅብረት ምርጫውን አልታዘብም ከማለቱ በተጨማሪ በሚዲያ ላይ የተጫነው አፈና በዓለምአቀፉ የሰብዓዊ መብት ድርጅት ይፋ ከሆነ ወዲህ ማነቆው በኢህአዴግ ላይ እየከረረ መምጣቱን ያሳያል፡፡ ኢህአዴግን ለሥልጣን ከማብቃት አልፋ ነፍጥ አንጋቢዎቹን የህወሃት መሪዎች ጸጉርና ጺም ከርክማ፤ ልብስ አልብሳ፤ ቋንቋ አስተምራ፤ የከተማ አኗኗር እንዴት እንደሆነ አሠልጥና፣ ቶሎ ባይገባቸውም ፕሮቶኮል አስተምራ፣ እስካሁንም ተንከባክባ እዚህ ድረስ ያቆየቻቸው እንግሊዝ እንዲህ ያለውን የውጭ ምንዛሪ ምንጭ ስታደርቅ “ቀጣዩስ ምን ይሆን?” የሚል ጥያቄ እንዲነሳ አድርጓል፡፡ “ምዕራባውያን መግደልም ማንሳትም ያውቁበታል” በማለት አስተያየት የሚሰጡ ወገኖች እንደሚሉት ቀጣዩ የኢህአዴግ ጉዞ በከፍተኛ ሁኔታ ለህወሃት ሲቀጥል ለኢህአዴግ አስጊ ከመሆን ባሻገር በውጭ ምንዛሪ እጥረት በየጊዜው የሚፈጠረውን ግሽበት በዕርዳታ ገንዘብ የሚያስተካክለው ኢህአዴግ እንዲህ ያለው የገንዘብ ማዕቀብ ክፉኛ ያነጥፈዋል ሲሉ ግምታቸውን ይሰጣሉ፡፡ ሙስናው መረን በለቀቀባት አገር ከሕዝብ እየተዘረፈ በተለያዩ አገራት ባንኮች በውጭ ምንዛሪ የሚከማቸውን ገንዘብ በሚካፈሉትም ላይ የድርሻ ቅነሳ የማስከተሉ ጉዳይ አብሮ የሚታይ እንደሆነ ይነገራል፡፡

ከዚህ ዜና ጋር ተያያዥነት ያለውን ጥቅምት 2፤2005 (October 12, 2012) ያተምነውን ዜና ከዚህ በታች እንደሚከተለው እንደገና አትመነዋል፡፡

ኢህአዴግ በ600 ሚሊዮን ዶላር አጣብቂኝ ውስጥ ገባ!!

ብያኔው ከጸና ኪሣራው በቢሊዮን ዶላር ሊደርስም ይችላል!

ኢህአዴግ ከዓለም ባንክ ያገኘውን 600 ሚሊዮን ዶላርና በተመሳሳይ ፕሮጀክት ወደፊት ሊያገኝ የሚችለውን ከፍተኛ ገንዘብ በተመለከተ አደጋ ውስጥ መውደቁ ተሰማ። ኢንስፔክሽን ፓናል (Inspection Panel – IP) የተሰኘ ተቋም ይፋ ያደረገው መረጃ እንደሚያመለክተው ኢህአዴግ የቀረበበት ውንጀላ ከተረጋገጠ የሚያጣው ገንዘብ በቢሊዮን ዶላር እንደሚደርስ ታውቋል። ይፋ የሆነውን መረጃ አስመልክቶ ከኢህአዴግ ወገን እስካሁን በይፋ የተሰጠ ምላሽ የለም።

ግፍ የሚፈጽሙ መንግስታትን፣ በልማት ስም የሰብዓዊ መብት ጥሰት የሚፈጽሙ ወንጀሎችን መረጃዎችን በስፍራው በመገኘትና ከመሠረቱ ዘልቆ በመግባት አደራጅቶ ተጠያቂ የሚያደርገው ኢንክሉሲቭ ዴቨሎፕመንት ኢንተርናሽናል Inclusive Development International (IDI) ከሰለባዎቹ ውክልና ተሰጥቶታል። ተቋሙም በውክልናው መሰረት ለኢንስፔክሽን ፓናል በዝርዝር የሰለባዎቹን በደል በማተት አሳውቋል።

የኢህአዴግ መከላከያ ሠራዊት የሚያደርሰውን እስራት፣ ግርፋት፣ አስገድዶ መድፈር፣ ከመኖሪያ ቦታ ማፈናቀል፣ የግዳጅ ሰፈራ ወዘተ በማምለጥ ወደ ኬንያ የተሰደዱ የጋምቤላ ነዋሪዎች ይህ ሁሉ ግፍ የሚፈጽምባቸው የኢትዮጵያ መንግሥት በልማት ስም ከዓለም ባንክ በሚያገኘው የዕርዳታ ገንዘብ በመሆኑ ለባንኩ በላኩት የአቤቱታ ደብዳቤ አመልክተዋል።

አቤቱታውን መሠረት በማድረግ የሚደረገው ምርመራ ውጤት ይፋ ሲሆን፣ በሌሎች አገሮች እንደተደረገው በዕርዳታ ስም የሚገኝን ገንዘብ ኢህአዴግ ለፖለቲካ ተግባር መጠቀሙ ሲረጋገጥ፣ በመስከረም ወር መጀመሪያ አካባቢ ከዓለም ባንክ ተፈቅዶ የነበረው 600ሚሊዮን ዶላር ሊከለከል ይችላል፡፡

የዛሬ ዘጠኝ ዓመት አካባቢ በሟቹ ጠ/ሚ/ርና የጦር ኃይሎች ጠቅላይ አዛዥ መለስ ዜናዊ ቀጥተኛ ትዕዛዝ በጋምቤላ ክልል በተለይ የተማሩ ወንዶች ላይ በማተኮር 424 ንጹሐን የአኙዋክ ተወላጆች በተገደሉበት ወቅት በሺዎች የሚቆጠሩት ወደ ጎረቤት አገር ኬንያ መሰደዳቸው ይታወሳል፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ክልሉ ሰላም የለም፡፡ በየጊዜውም የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ሲካሄዱበት ቆይቷል፡፡ በተለይም ለም የሆነውን እጅግ ሰፋፊ መሬት ለውጪ ባለሃብቶች በሳንቲም በመሸጥ ላይ የሚገኘው የኢህአዴግ አገዛዝ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በቀድሞው የደርግ ዘመን ሲካሄድ ከነበረው ባለፈ መልኩ እጅግ በሚያሰቅቅ ሁኔታ በመንደር ምስረታና አስገድዶ የማስፈር ፖሊሲ ከመኖሪያ ቀዬ የማፈናቀል ተግባራትን እያከናወነ መሆኑን የኦክላንድ ተቋም፣ ሂውማን ራይትስ ዎች፣ … የመሳሰሉ ድርጅቶች ያወጧቸው ዘገባዎች ይጠቁማሉ፡፡

ከ1998ዓም ጀምሮ የመሠረታዊ አገልግሎት ጥበቃ ፕሮግራም (Protection of Basic Services “PBS Program”) በሚል በአራት ተከታታይና ሁለት ተጨማሪ የገንዘብ ድጎማ የሚደረግባቸውን ፕሮግራሞች የዓለም ባንክ በኢትዮጵያ ሲያካሂድ ቆይቷል፡፡ ይህ መሠረታዊ የሆኑ አገልግሎቶችን ለማሟላት ተወጥኖ የሚካሄድ ፕሮጀክት በትምህርት፣ በጤና፣ በእርሻ፣ በንጹህ ውሃ አቅርቦት፣ በገጠር መንገድ ሥራ፣ ወዘተ መስኮች ላይ እንዲውል (PBS I, PBS I-AF (Additional Financing), PBS II, PBS 11-AF, PBS-Social Accountability Program and PBS III) በማለት በተለያዩ ደረጃዎች ለተከፋፈለው ኦፐሬሽን ማስፈጸሚያ የሚውለው ገንዘብ ከ13ቢሊዮን ዶላር የሚበልጥ ነው፡፡ ከዚህ ውስጥ ከፍተኛው የዓለም ባንክ ድርሻ 2ቢሊዮን ዶላር ሲሆን የተቀረው በሌሎች ለጋሽ መንግሥታት እና ድርጅቶች የሚሸፈን ነው፡፡ PBS III የተሰኘውን በሦስት ንዑሳን ፕሮግራሞች የተከፋፈለውን ፕሮጀክት ለማስፈጸም በአጠቃላይ የሚፈጀው 6.3ቢሊዮን ዶላር በላይ ነው፡፡ ከዚህ ውስጥ የባንኩ ድርሻ የሆነውን 600ሚሊዮን ዶላር ቦርዱ መስከረም 5ቀን 2005ዓም አጽድቋል፡፡

በአስገድዶ ማስፈር፣ መንደር ምስረታና ሌሎች በርካታ የሰብዓዊ መብቶቻቸው የተጣሱባቸው በኬንያ የሚገኙ ሦስት የአኙዋክ ስደተኞች ተወካይ ድርጅቶች በሰሜን አሜሪካ ከሚገኙ ሌሎች የሰብዓዊ ድርጅቶች ጋር በመሆን ባንኩ ሊሰጥ የወሰነውን ገንዘብ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ጥቅም ከመዋል ይልቅ ለኢህአዴግ የፖለቲካ ዓላማ ማስፈጸሚያ እየዋለ መሆኑን በመጥቀስ ለባንኩ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ጂም ዮንግ ኪም መስከረም 6፤ 2005ዓም ደብዳቤ ልከዋል፡፡ በጥያቄያቸውም መሠረት በዓለም ባንክ በኩል ወደ ኢትዮጵያ የሚፈሰው ገንዘብ “በልማት ስም የኢትዮጵያ መንግሥት በጋምቤላ ክልል ለሚያካሂደው የመንደር ምስረታ እየዋለ ነው” በማለት ይከሳል፡፡ ሲቀጥልም የአኙዋክ ሕዝብ ለዘመናት ከኖረበት መንደር በማፈናቀል “የተሻለ አገልግሎትይሰጣችኋል” በማለት በግድ የማስፈር ተግባር እየተፈጸመ ሲሆን “የተባለው አገልግሎትም ሆነ ለእርሻ የሚሆን በቂ ቦታ እንዲሁም ለከብቶች የሚበቃ የግጦሽና የውሃ ቦታ የላቸውም” በማለት ሰፈራውን የተቃወሙ ሁሉ እጅግ ከፍተኛ የሆነ የሰብዓዊ መብት ረገጣ እየደረሰባቸው እንደሚገኝ ጠቁሟል፡፡ ይህንን ግፍ የሚፈጽሙት ደግሞ የዓለም ባንክ ለመሠረታዊ አገልግሎት ጥበቃ ፕሮግራም (Protection of Basic Services “PBS Program”) ስም ለልማት እንዲውል ከሚሰጠው የዕርዳታ ገንዘብ በመንግሥት ተቀጥረው ደመወዝ የሚከፈላቸው ሠራተኞች መሆናቸውን ገልጾዋል፡፡ ይህንን ጉዳይ ከዓለም ባንክ ጋር እንዲነጋገሩላቸው Inclusive Development International (IDI) የተባለውን ድርጅት መወከላቸውን አስታውቀዋል፡፡ (የደብዳቤው ሙሉ ቃል እዚህ ላይ ይገኛል)

ተመሳሳይ ጉዳዮችን በዓለምአቀፍ ደረጃ በመከታተልና በማስፈጸም የታወቀው IDI በመስከረም ወር አጋማሽ ላይ ጉዳዩ በቀጥታ ለሚመለከተው የመልሶ ማቋቋምና ልማት ዓለምአቀፍ ባንክና (International Bank for Reconstruction and Development (IBRD)) የዓለምአቀፍ ልማት ማኅበር (International Development Association (IDA)) ሥር ለሚገኘው የኢንስፔክተር ፓናል ባለ 18ገጽ ደብዳቤ ጽፏል፡፡ (የደብዳቤው ሙሉ ቃል እዚህ ላይ ይገኛል) ይህ የኢንስፔክተር ቡድን ከፍተኛ ሥልጣን ያለው መ/ቤት ሲሆን የዓለም ባንክ የሚሰጠውን ገንዘብ በትክክለኛ ቦታ ላይ አለመዋሉን በመጥቀስ ክስ የሚያቀርቡ ወገኖችን ጉዳይ በመከታተልና ቦታው ድረስ የራሱን ምርመራ በማካሄድ ውጤቱ ተግባራዊ እንዲሆን የባንኩን እጅ የማስጠምዘዝ ዓቅም ያለው እንደሆነ ከዚህ በፊት ያካሄዳቸው የምርመራ ውጤቶች ይጠቁማሉ፡፡

ይህ የመርማሪ ቡድን የቀረበለትን አቤቱታ መቀበሉንና በጉዳዩ ላይ የማንም ተጽዕኖ የማይደረግበትን የራሱን ምርመራ እንደሚያደርግ ከትላንት በስቲያ ባወጣው ባለ 8ገጽ መግለጫ ላይ አሳውቋል፡፡ ይህ የአቤቱታ ፋይል ቁጥር የተሰጠው ጉዳይ በግልባጭ ለባንኩ ፕሬዚዳንትና ለከሳሽ ተወካይ ድርጅት (IDI) እንዲደርስ ተደርጓል፡፡(የደብዳቤው ሙሉ ቃል እዚህ ላይ ይገኛል)

የጎልጉል የሰሜን አሜሪካ ዘጋቢ ባጠናከረው መረጃ መሠረት ቡድኑ ከያዝነው ዓመት የጥቅምት አጋማሽ በኋላ ወደ ምስራቅ አፍሪካ ያቀናል። ቡድኑ ስደተኞቹ የሚገኙባቸውን፣ እንዲሁም ጉዳዩን በሚመለከት አስፈላጊ የሚላቸውን ቦታዎችና ግለሰቦች ሙሉ በሙሉ ያነጋግራል። ለስራው መሳካት የሚሆነውን ሁሉ በሚፈለግበት ቦታ በመገኘት በግንባር እንደሚያከናውን ለማወቅ ተችሏል።

በተለያየ ጊዜ ኢህአዴግ የሚፈጽመውን ግፍና በደል በማደራጀት ሥርዓቱ ላይ ከትጥቅ የጠነከረ ትግል ማካሄድ እንደሚቻል አስተያየት ሰጪዎች ተናግረዋል:: አያይዘውም በመላው አገሪቱ የሚፈጸመውን የሰብአዊ መብት ረገጣና የመብት ጥሰት በማሰባሰብ የኢህአዴግን የገንዘብ ምንጭ የማድረቅ፣ ብሎም በእርዳታ ገንዘብ የሚገነባቸውን የአፈና ተቋማት ማስለል እንደሚቻል አስታውቀዋል። ይህንን ታላቅ ስራ የሰሩትን አካላት ልምዳቸውን ለሌሎች በማካፈል አስፈላጊውን ስራ ሊሰሩ እንደሚገባም አሳስበዋል። (የመግቢያው ፎቶ የተወሰደው: ዘጋርዲያን)

Source: ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ

– See more at: http://satenaw.com/amharic/?p=4974#sthash.PE1Xev8t.dpuf

ሰበር ዜና፣ የወያኔ ሰላይ ከሆላንድ ተባረረ!

ሂሩት መለሰ – ከሮተርዳም

ሮተርዳም፣ ጥቅምት 28 ቀን 2015 – በስደት ስሙ አለማየሁ ስንታየው በመባል የሚታወቀው የህወሃት ሰላይ ከኔዘርላንድስ ተባረረ። አለማየሁ ስንታየሁ ቋሚ ነዋሪ ከነበረበት ከኔዘርላንድስ እንዲባረር የተደረገው በዚያ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን በከፈቱበት የስለላ ክስ መሆኑም ታውቋል።

TPLF spy in Netherlands

የሮተርዳም ከተማ ፍርድ ቤት በአለማየሁ ላይ የተመሰረተውን የስለላ ክስና ማስራጃ ለረጅም ጊዜ ሲመረምር ከቆየ በኋላ የግለሰቡ የመኖርያ ፈቃድ እና ቤት እንዲነጠቅ፣ የሆላንድን ምድርም በአስቸኳይ ለቆ እንዲወጣ ውሳኔ አስተላልፏል። ከሆላንድ የምመራ ቡድን እንደተረዳነው ከሆነ – የግለሰቡ ቤት ሲፈተሽ ወያኔ የሰጠው እውነተኛ መታወቂያ እና በርካታ የስለላ ሰነዶች ተገኝተውበታል። በእርዳታ ስም የተቋቋመለት ድርጅትም ተፈትሾ ማስረጃዎች እንደተገኙ ለማወቅ ተችሏል።

ይህ ሰው ትክክለኛ ስሙ ዘለቀ ፎላ ይባላል። በደርግ ጊዜ የኢትዮጵያ ሰራዊት አባል ሆኖ ለረጅም አመታት አገልግሏል። ወያኔ ስልጣን ሲቆጣጠር ለፖለቲካ ተሃድሶ አዋሳ ደቡብ ጦር ቅጥር ግቢ ተላከ። በተሃድሶ በነበረበት ጊዜ ቁጥራቸው ብዙ የሆኑ የሰራዊቱ አባላትን ለወያኔ በማጋለጥ ታማኝነቱን ሲያሳይ እንደነበር የዚህ ዜና ዘጋቢ እማኝ ነው። የበርካታ ኢትዮጵያውያን ደም በእጁ ያለው አለማየሁ ከተሃድሶው ከወጣ በኋላ እስራኤል ገደቡ (የፓልቶክ ስሙ ኢዛና) ከተባለ ወታደር ጋር በመሆን የሰላም ተጓዥ ነኝ ብሎ በመገናኛ ብዙሃን ሲታይ ነበር። አለማየሁ እና ኢዛና በየሃገሩ እየዞሩ ስለ አዲሱ ስርዓት መልካምነት ሲሰብኩ ከረሙ። ከዚያም አስመራ ድረስ ተልከው የሻእቢያውን መሪ ኢሳያስ አፈወርቂን በወታደሩ ስም ይቅርታ ጠይቀዋል።

TPLF spy in Netherlands

አለማየሁ እና ኢዛና ለወያኔ በሰሩት ውለታ ሆላንድ ገብተው እንዲቀሩ ተደረገ። ይህም የተደረገበት ምክንያት በአውሮፓ የሚኖሩ ኢዮጵያውያንን ተቃዋሚ በመምሰልና በረቀቀ መንገድ እንዲያበጣብጡና እንዲሰልሉ ነው።

በሆላንድ ሃገር የፖለቲካ ጥገኝነት ጠይቆ ለወያኔ ቡድን የስለላ ስራ መስራት ወንጀል ነው። አለማየሁ የሆላንድ ዜግነት ቢኖረው ኖሮ ቅጣቱ የከፋ ይሆን እንደነበር ጉዳዩን እየተከታተሉ ያሉ የህግ ባለሙያዎች ተናግረዋል።

የአለማየሁ መባረር በተሰማ ግዜ በሮተርዳም ያሉ የህወሃት ደጋፊዎች የአቤቱታ ደብዳቤ በመጻፍ ፊርማ ማሰባሰብ ቢጀምሩም ሊሳካላቸው አልቻለም። የአቤቱታ ደብዳቤው ግለሰቡ እዚህ የተወለዱ ሁለት ለጆቹን እየመጣ እንዲጎበኝ ይፈቀድለት የሚል ነበር።

አለማየሁ ስንታየሁ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ከሆላንድ ተባረረ። ኢዛና ግን አሁን የተቃዋሚ ጭንብሉን አውልቆ በግልጽ ወያኔ መሆኑን መናገር ጀምሯል። ኢዛና የሆላንድ ዜግነት ቢኖረውም በሆላንድ ሃገር ስራ ሰርቶ አያውቅም። የቀንና ማታ ስራው በፓልቶክ ላይ ነው። ባለፈው ወር ኢትዮጵያ የተጓዙ ዲያስፖራ ኢንቨስተሮችን እየመራ በቴሌቭዥን መግለጫ ሲሰጥ አይተነዋል። ይህ ትርኢት የወያኔ ኢንቨስተሮች በጨበጣ እንደሚንቀሳቀሱም ያሳየናል።

ስለ አለማየሁ ስንታየሁ የበለጠ ለማወቅ ይህችን ሊንክ ይጫኑ፡

http://ecadforum.com/blog1/expose-tplf-agents-masquerading-as-refugees-within-the-ethiopian-diaspora/

የአድዋ ድልና ትሩፋት ፈተናዎቹ – ሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው

ሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው


በእርግጠኝነት ኢትዮጵያዊ ልብ ላለው ሰው ሁሉ ስለ አድዋ ድል ሲሰማና ሲያወራ ልቡ በኩራት ይሞላል መንፈሱ ይነቃቃል፡፡ ኢትዮጵያዊ ብቻም አይደለም በየትኛውም ዓለም ያለ በቅኝ ግዛት ቀንበር ፍዳ ያየ የትኛውም የሰው ዘር ጭምርም እንጅ፡፡ ይህን አንጸባራቂ ድል መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ በአንድነት ተሰልፎ ካስመዘገበ እነሆ ነገ የካቲት 23 ቀን 2006ዓ.ም 118 ዓመቱን ይይዛል፡፡ ይህንን ድል ለመቀዳጀት ፈተና የነበሩት ነገሮች ምን ምን ናቸው? ለመሆኑ ይህ ድል እንዴት ተገኘ ?  የዚህ ታላቅ ድል ትሩፋቶችስ ምን ምን ናቸው? የዚህ ድል ጠላቶች እነማን ናቸው? ይህ ድል እንዴት ይጠበቃል? ብዙ ቢባልለት ከማይበቃው ከአድዋ ድል እነዚህን ነጥቦች ብቻ ነጥለን ለማየት እንሞክራለን፡፡

ዐፄ ምኒልክ ምታ ነጋሪት ክተት ሠራዊት ብለው ፋሽስት ጣሊያን በዘመነ ዐፄ ዮሐንስ 4ኛ ከነበረበት አልፎ የትግሬ ገዥ የነበሩትን ዐፄ ዮሐንስ 4ኛ ከእሳቸው ቀጥለው እንዲነግሡ በማሰብ ሊሞቱ በሚያቃትቱበት ወቅት ወራሸ ነው ለእኔ ያደረጋችሁትን ሁሉ ለእሱም አድርጉ በማለት ተናዘውላቸው የነበሩትን ራስ መንገሻን ድል አድርጎ ሠራዊታቸውን ከበተነ በኋላ አልፎ መላዋን ሀገራችንን ቅኝ ለመግዛት ወደ መሸገባቸው ቦታዎች ወደ አንባ አላጌ፣ መቀሌ እንዳኢየሱስና አድዋ ከመዝመታቸው እነዚያን አኩሪ ድሎች ከማስመዝገባቸውና ታሪክ ከመሥራታቸው በፊት እነኝህን ድሎች እንዳንቀዳጃቸው የሚያደርጉ እጅግ ከባባድ ፈተናዎች ተጋርጠውብን ነበር፡፡ የአድዋን ድል በሌሎች ሀገራት ከተገኙት ድሎች ልዩ የሚያደርገውም ይሔው ነው፡፡ እነዚህ ፈጽሞ ሊታለፉ የማይቻሉ መሰናክሎችን ታልፎ የተገኘ ድል በመሆኑ፡፡

የአድዋን ድል ለመቀዳጀት አያስችሉ የነበሩት ፈተናዎች ምን ምን ናቸው፡- 

  1. የከብት እልቂት፡- ፋሺስት ጣሊያኖች ኢትዮጵያን ቅኝ ለመያዝ ሲያስቡ ቅኝ ገዥዎች በአፍሪካና እስያ በቀላል ግጭት ቅኝ ሀገር መያዝ እንደቻሉ ሁሉ በኢትዮጵያ ይህ መልካም እድል እንደማያጋጥማቸው ጠንቅቀው ዐውቀውት ነበር፡፡ በመሆኑም ጦርነት መግጠማቸው የማይቀር ከሆነ የኢትዮጵያንና የመንግሥቷን አቅም ለማዳከም የሚያስችል ስልት ነደፈ ከስልቶቹ አንዱም የሀገሪቱ ሀብት መሠረት የሆነውን ግብርናዋን ማሽመድመድ መጉዳት ነበር፡፡ ይህንን ሲያስቡ ግብርናዋን ለመጉዳት ማድረግ የሚችሉት ነገር ሆኖ ያገኙት የከብት ሀብቷን መጨረስ ነበር፡፡ ይህንን ለመፈጸም ሲባል ከህንድ ሀገር ሶስት የታመሙ ከብቶችን በምጽዋ በኩል አስገብተው ከደማቸው እየወጉ የኞቹን ደኅናዎቹን ከብቶች በመውጋት አጋቡባቸው በሽታውም በአጭር ጊዜ ተዛምቶ ከኢትዮጵያም አልፎ አጠቃላይ የቀጠናውን ከብት ፈጀው፡፡ ውጤቱም ፋሽስቶቹ ከጠበቁት እጅግ የበዛ ሆኖ በሀገራችን ታሪክ ታይቶ የማይታወቅ ‹‹ክፉ ቀን›› በመባል የሚታወቀውን ረሀብና ችጋር አመጣ፡፡ የሚበላ ነገር ጠፍቶ ዋልካ አፈርና ሳር ቅጠሉ ሁሉ የተበላበት ዘመን ነበር፡፡ ሕዝቡ ደቀቀ አለቀ ሀገሪቱ ተሽመደመደች፡፡
  2. የስንቅና ትጥቅ (logistics) ዝግጅት እጅግ ውስንነት፡- ፋሽስት ጣሊያን በወቅቱ ኃያላን ከሚባሉ የአውሮፓ ሀገራት አንዱ ነበረ፡፡ እንደ ኃያልነቱም ከ20 ሺ በላይ ለሆነው ላሰለፈው ጦሩ ዘመናዊ መሣሪያ በነፍስ ወከፍ ከማስታጠቁም ባሻገር ሠራዊቱ በወጉ የተደራጀ ዘመናዊ የውትድርና ሥልጠና የወሰደ ባጠቃላይ ከበቂ በላይ የስንቅና ትጥቅ ዝግጅት የነበረው ነበር፡፡ በእኛ በኩል የነበረው ደግሞ ባጋጠመው የረሀብና አስከፊ ችጋር የደከመ ሠራዊት ከመሆኑም በላይ ከፍተኛ የሆነ የስንቅና ትጥቅ አቅርቦች ችግር ነበረበት፡፡ በወቅቱም ሠራዊቱ ነፍሱን ለማቆየት በቀን እጅግ መጥኖ ከሚቀምሳት በየ አገልግሉ ቋጥሮ ከያዛት ጥቂት ዳቦቆሎ፣ የደረቀና የሻገተ ቂጣ፣ ቆሎና በሶ የመድኃኒት ያህል ጥቂት ጥቂት የሚቀምስ ሠራዊት ነበረ እንጅ የስንቅ አቅርቦቱን አስቦ በየ ዕለቱ አብስሎ የሚያቀርብለት አካል አልነበረም፡፡ ሰራዊትም ሲባል ሐበሻ እንዲያው በተፈጥሮው ተዋጊ በመሆኑ እንጅ ሊገጥመው እንደተዘጋጀው ጠላቱ ሠራዊት በወጉ የወሰደው የውትድርና ትምህርት ጨርሶ አልነበረም፡፡ የታጠቀው መሣሪያም ቆመህ ጠብቀኝ በሚባል የሚታወቁ ኋላ ቀር መሣሪያ ሆኖ ይሄንንም ቢሆን የያዙት ከሠራዊቱ እጅግ ጥቂቶቹ ነበሩ የተቀረው ግን የያዘው ጦርና ጋሻ ጎራዴ ነበር፡፡ ይሔም አይጠቅምም ማለት ሳይሆን በጦር በጎራዴና በጋሻ ውጊያ የሚደረግበት ዘመን አልፎ ከሩቁ ጠላትን መልቀም ማስቀረት የሚቻልባቸው ከመድፍ እስከ መትረየስ ያሉ ዘመናዊ መሣሪያዎች የወጡበት ዘመን በመሆኑ ለሚደረገው ጦርነት የጦር የጎራዴ እና የጋሻ ጥቅምና አገልግሎት እጅግ በጣም ውስን ሆኖ ነበር፡፡ ጦርነት በጦር በጎራዴ ይደረግ የነበረበት ዘመን ለእኛ እጅግ የቀና የበጀና የሰለጠም ነበር፡፡
  3. የባንዶች ሚናና የጠላት የመከፋፈል ስልት፡- ፋሽስት ጣሊያን የኢትዮጵያን ሠራዊት ለማዳከም ከተጠቀመበት ስልት ሌላኛው ባላባቶችንና መሳፍንቱን እስከ ራሶች ድረስ እንዲከዱ በማድረግ ከጎኑ ማሰለፍ ነበር፡፡ ጥቂት የማይባሉትንም ማስካድ ችሎ ነበር ነገር ግን እነዚህ የከዱና ከነሠራዊታቸው በባንድነት የተሰለፉ መኳንንት የጠበቁትንና የፈለጉትን አቀባበልና መስተንግዶ እንዳላገኙና እንደማያገኙም ሲገባቸው የዐፄ ምኒልክ ይቅር ባይነት ዋስትና ሆኗቸው ብዙዎቹ ተመልሰዋል፡፡ ይሁን እንጂ እነኝህ ከድተው የነበሩ ሹማምንት መመለሳቸው የእውነት ከልብ ነው ወይስ ለተልዕኮ? የሚለው ጉዳይ ለወገን ሠራዊት በወቅቱ እጅግ አንገብጋቢ ጥያቄና እውነቱን ለመረዳት ከመቸውም አጋጣሚ በበለጠ አምላክነትን የሚያስመኝ፤ ሥጋት ጥርጣሬውም እረፍትና እንቅልፍ የሚነሳ አምኖ ለማሰለፍም ለመተውም ያስቸገረበት ጉዳይ ሆኖ ነበር፡፡
  4. የፋሽስት ጣሊያን ጦር መሽጎ ያለ መሆኑ፡- ጦርነት በሚደረግበት ወቅት ጦርነት ከሚያደርጉት ባላንጣ አካላት አንደኛው ምሽግ ይዞ የሚጠብቅ ከሆነ ጦርነቱ ለአጥቂው ወይም ምሽግ ላልያዘው ክፍል እጅግ ከባድና አስቸጋሪ የሚያስከፍለው ዋጋም ከመሽገው አካል ጋር ሲነጻጸር በጣም የሚበዛ መሆኑ የማይቀር ነው፡፡ እኛንም ያጋጠመን ይሄው ነበር በሶስቱም ቦታዎች የጠላት ጦር ምሽጉን በሚገባ ገንብቶ ከምሽግ ማዶም በባዶ እግሩ የሚጓዘውን አርበኛ ሠራዊት እንዲቆራርጥ በጠርሙስ ስብርባሪና በጦር ችካሎች ከዚያም በፈንጂ የታጠረ ምሽግ ውስጥ ሆኖ አድፍጦና መሽጎ ይጠብቅ የነበረ ጦር ከመሆኑ የተነሣ የጠላትን ጦር ከዚህ ምሽጉ ለማስወጣት ምን ያህል መሥዋዕትነት ሊጠይቅና ሊያስከፍል እንደሚችል መገመት ይቻላል፡፡ እንኳንና ተመጣጣኝ ትጥቅ ሳይያዝ ቢያዝም እንኳ ሁኔታው እጅግ ከባድ ነው በዚህ ላይ የእኛ ጦር ዘመናዊ የውጊያ ስልት ካለመማሩ ጋር ተያይዞ ተኝቶ መሬት ላይ በመሳብ መተኮስን እንደ ነውርና ፈሪነት አድርጎ የሚቆትር በመሆኑ ደረቱን ሰጥቶ በከፍተኛ ድፍረትና ወኔ ይዋጋ የነበረ ጦር ከመሆኑ ጋር ተያይዞ መሥዋዕትነቱን እጅግ የከበደ አድርጎት ነበር፡፡ የሚገርመው ነገር ግን ከነዚህ ነባራዊ ሁኔታዎች አኳያ ከጦርነቱ በኋላ የደረሰብን የሟችና ቁስለኛ መጠን በጠላት ሠራዊት ከደረሰው እምብዛም የሚበልጥ አልነበረም፡፡
  5. የህክምና አገልግሎት ችግር፡- እንዲህ ዓይነት የሕዝብ እንቅስቃሴ በሚደረግበት ወቅት ወረርሽኝ ይከሰታል፡፡ ወረርሽኝ ሲከሰትም ለዚህ ጉዳይ ቀድሞ የተዘጋጀ ህክምና ከሌለ ከባድ ጥፋት አስከትሎ ያልፋል፡፡ የወገን ጦር ይሔንን አደጋ መከላከል የሚችልበት አቅምና ዝግጅት አልነበረም ሌላው ቀርቶ ቁስለኛን እንኳን ማከም የምንችልበት መድኃኒትና ባለሙያ አልነበረንም ሁሉም ለየራሱ ሐኪም ነበረ፡፡ አስተናግር ቅጠሉን ጨምቆ አዘጋጅቶ ይዞት የመጣውን ቁስሉ ላይ እያፈሰሰ እርስ በራሱ ለመተካከም ይሞክራል እንጅ ይሔንን ጉዳይ የሚከውን የህክምና ቡድን አልነበረም፡፡

እንግዲህ እነዚህና ሌሎች ሊታለፉ የማይችሉ እንደተራራ የገዛዘፉ ከባባድ ደንቀራዎችን ፈተናዎችን በእግዚአብሔር ቸርነት በሐበሻነት ጽናት እናት አባቶቻችን አልፈው ነው የአንባላጌውን፣ የመቀሌውን፣ በመጨረሻም የአድዋን ድል ለመቀዳጀት የቻሉት፡፡ የአድዋ ድል በሌሎች ዜጎች ዘንድም በከፍተኛ አድናቆት የሚደነቀው የሚከበረውም ከዚህ የተነሣ ነው፡፡

ለመሆኑ ይህ ድል እንዴት ሊገኝ ቻለ?፡- ለድሉ መገኘት ትልቁ ድርሻ የእግዚአብሔር ረድኤት ቢሆንም እግዚአብሔር ሲሠራ በምክንያት ወይም መሣሪያ የሚያደርገው ነገር መኖሩ አይቀርምና ለእናት አባቶቻችን ቁርጠኝነትን፣ ጽናትን፣ መጨከንን ሰጥቶ ከቶውንም የማይታለፉትን ፈተናና መከራን አስተናግዶም በእነሱም ደክሞ ደቆ የነበረ ሕዝብ ተሰባብሮ ተነሥቶ እንዲህ ዓይነት አስደናቂ ድል ለማስመዝገብ በቃ፡፡ እንዲህ ዓይነቱን ድል ለማስመዝገብ ሐበሻ ሆኖ መገኘትን የግድ ይጠይቅ ነበር አደረግነውም፡፡ በመሆኑም “ነፃነት ወይም ሞት” “ባሪያ ሆኖ ከመኖር ነፃ ሆኖ መሞት” የሚለው የጨከነ መርሑ ከፊቱ የተደቀኑ ግዛዙፍ ፈተናዎችን መሰናክሎችን ከነ አካቴው ከግምት ውስጥ እንዳያስገባ አድርጎት በከፍተኛ ቁርጠኝነትና ጽናት በመዋጋቱ ድሉን ሊያገኝ ቻለ፡፡

የዚህ ታላቅና አንጸባራቂ ድል ትሩፋቶች ምን ምን ናቸው? ይህ ታላቅ ድል ከእኛም አልፎ ለመላው ዓለም ጭቁኖች በርካታ ትሩፋቶችን አበርክቷል ከእነዚህ በርካታ ትሩፋቶቹ ጥቂቶቹን ለመጥቀስ ያህል፡-

  1. የቀለም ልዩነትን መሠረት ያደረገው የብቃት ደረጃ ልዩነት አስተሳሰብን ፉርሽ መሆኑን ማረጋገጥ ችሏል፡፡ ከዚህ ድል አስቀድሞ ጥቁር ሲባል ሰብአዊ እሴት አልባ፣ ለባርነት የተፈጠረ፣ ሥልጣኔ የማይገባው አድርገው ያስቡት ነበር፡፡ ከዚህም አልፈው ተናጋሪ እንስሳ እያሉ ይገልጹት ነበር፡፡ ጥቁሮቹ እናት አባቶቻችን ግን ፈጽሞ ሊታለፉ የማይቻሉ ፈተናዎችን አልፈው ለክብራቸው ለነፃነታቸው፣ ለሉዓላዊነታቸው የማይችሉት ነገርም እንኳን ቢሆን አንችለውምና ምን እናድርግ ብለው ክብራቸውን፣ ነፃነታቸውን፣ ሉዓላዊነታቸውን ለድርድር ሳያቀርቡ ለሰብአዊ ክብራቸውና ለማንነታቸው ታይቶ በማይታወቅ ቀናኢነት በየትኛውም የዓለም ክፍል ያለ ማንኛውም ዓይነት የሰው ዘር አደርገዋለሁ ብሎ ሊሞክረው ቀርቶ ሊያስበው በማይችለው ሁኔታ በግሩም ችሎታና የአጨራረስ ብቃት ከውኖ በማሳየቱ ጥቁር እንዲህ እንዲህ ነው እየተባለ ዝቅ ተደርጎ ይቆጠርና ይታይ የነበረው አስተሳሰብ የተሳሳተ መሆኑን የግዳቸውን እንዲያምኑ አድርጓል፡፡
  2. የነፃነት ትግልን አነቃቅቷል ቀስቅሷል፡- ጥቁር አፍሪካዊያን ለአምስት ምእተ ዓመታት ያህል በግፈኛ ነጮች ሲሰበክላቸው የኖረውን የጥቁርን ተገዥነት ወይም ለአገልጋይነት መፈጠር አምኖ ተቀብሎ ሰጥ ለበጥ ብሎ የመገዛትን አስተሳሰብ አዳብሮ ወደ አውሮፓና አሜሪካ እየተጋዘ እየተሸጠ እየተለወጠ ይገዛ ያገለግል ነበር፡፡ ሐበሾቹ ጥቁሮች አድዋ ላይ ያበሩላቸው ፀሐይ ግን ይሄንን የጨለመ አስተሳሰብ ጠራርጎ በማጥፋቱ የነጻነት ትግልንና የነፃነት ታጋዮችን በየስፍራው በየአቅጣጫው እንዲቀጣጠል አድርጎ እነሆ ዛሬ ላይ ያን ሁሉ ግፍ በጥቁርነቱ ብቻ ይጋት የነበረው የሰው ዘር ነጻነቱን አረጋግጦ ቢያንስ በገዛ ሀገሩ እንኳን እንደ ሰው መኖር የሚችልበትን ሁኔታ መፍጠር እንዲችል አብቅቷል፡፡
  3. የተረሳውን ታሪካችንን አስታውሷል፡- ሐበሻ እንደሕዝብና እንደ ሀገር ከማንም የቀደመ የሥልጣኔና የመንግሥት ታሪክ ያለውና የነበረው ሕዝብ ነው ይህ ግን በወቅቱ በነበረው አስገዳጅ ችግር ሳቢያ ከዐፄ ፋሲል ጀምሮ ለረጅም ጊዜ ቆይቶ በነበረው ዝግ መመሪያ (closed policy) ምክንያት ዓለም እኛን እኛም ዓለምን ረስተን ተረሳስተን ስለነበረ ዓለም በየጊዜው መረጃውን እያደሰ እንዳወቀን እዲቀጥል ማድረግ ሳንችል ቀርተን ነበር፡፡ የአድዋ ድል ግን ዓለም ስለኛ ያለውን መረጃ ካጎረበት እያወጣ እንዲያወራ እንዲህ እኮናቸው እንዲህእኮ ነበሩ እያለ እንዲያወራ አድርጎታል፡፡ ያወሩልን ይፅፉልን ከነበረው ታሪኮቻችን የሚበዛው እኛም እንኳን እራሳችን የማናውቃቸው ናቸው፡፡
  4. የሕዝባችንን አንድነት አጽንቷል፡- የጠላት ወረራ ለመኳንንቶቻችንና ለመሳፍንቶቻችን ትልቅ ትምህርትን ሰጥቷል፡፡ በአንድነት የመቆምን አስፈላጊነት የአንድነትን ጥቅም በሚገባ አስገንዝቧቸዋል፡፡ ከዚያ አስቀድሞ ከዘመነ መሳፍንት ጀምሮ በመሳፍንቱና በባላባቶች ዘንድ የየራሳቸውን ጎጥ እንደ ሀገር በመቁጠር የየራሳቸውን ‹‹ሀገር›› የመመሥረት የማይጠቅምና ኋላ ቀር አስተሳሰብ ያስቡ ነበር፡፡ ይህን የትም የማያደርስ አስተሳሰብ ለማጥፋት ዐፄ ቴዎድሮስን እጅግ አድክሟል፡፡ በዐፄ ቴዎድሮስ እጅ ያደጉት ዐፄ ምኒልክ 2ኛም የዐፄ ቴዎድሮስ 2ኛ ሕልም ገብቷቸው ስለነበር ጥረታቸውና ሁኔታዎች ፈቅደውላቸው የዐፄ ቴዎድሮስን ሕልም ለማሳካት ችለዋል፡፡ የአድዋ ድልም ለመሳፍንቱ የማይረሳ ትምህርትን ስለጣለላቸው ከዚያ በኋላ አስቀድሞ የነበረው ዓይነት የመሳፍንት አስተሳሰብ እንዳይኖር አድርጓል፡፡
  5. ለቀጣይ ትውልድ ታሪክ እንዴት እንደሚሠራና እንደሚጠበቅ ምሳሌነቱን ትቶ አልፏል፡- ሀገራችን ከ4500ዓመታት በላይ የመንግሥት ታሪክ አላት እንደ ሀገር ከቆመችበት ጊዜ ጀምሮ ነጻነቷን ለመንጠቅ ተደጋጋሚና አደገኛ ፈተናዎችን አሳልፋለች፡፡ እነዚሁ ጣሊያኖች በቀደመው ስማቸው ሮማዊያን ከቄሳሮች ዘመን ከሁለት ሽህ ዓመታት በፊት ጀምረው ሲፈታተኑን ኖረዋል፡፡ የአድዋ ድል እናት አባቶቻችን የዚህችን ሀገር ነጻነት እንደምን ባለ መሥዋዕትነት አስጠብቀው እንደቆዩና ይህ ረጅም ታሪኳ እንዴት እንደተሠራ የቅርብ ጊዜ ምሳሌነት የተወ ድል ነው፡፡ በደካማ ጎን መግባት የሚችሉበት ጠላቶቻችን ግን የትግል ስልታቸውን በቀጥታ ከሚተኮሰው አፈሙዝ ወደ ተለየ ዓይነት በመለወጥና ባንዶችን በማሠማራት የአድዋ ድል ከተወልን ምሳሌነት ልንማርና እኛም የድርሻችንን ታሪክ ልንሠራ የምንችልበትን ዕድል አጥበውት ሀገርን፣ አንድነትን፣ታሪክን፣ ነጻነትን፣ ሉዓላዊነትን፣ ክብርን መሠረቱ ያላደረገ የየግል ዓላማና አስተሳሰብ አራጋቢዎች አድርገውን አንድነታችንን አደጋ ላይ ጥለውታል፡፡በዚህ ረገድ እየተሳካላቸው ይገኛል፡፡ ፈጣሪ ይቅደምልን እንጂ የዚህ ውጤት ደስ የሚያሰኝ አይሆንም፡፡
  6. የታሪክ ሀብትን ትቶልናል፡- አንዲት ሀገር ዜጎቿ ጠንካሮች ከሆኑ ሁለቱም ሀብቶች ይኖሯታል ቁሳዊና መንፈሳዊ ሀብቶች ታሪክ መንፈሳዊ ሀብት ነው፡፡ ታሪክ መነቃቃትን የሚፈጥር ታላቅ ኃይል ነው፡፡ ቁሳዊ ሀብትም የመፍጠር ዐቅም አለው፡፡ ሀገራችን ኢትዮጵያ ሁለቱም ሀብቶች ነበሯት፡፡ ነበሯት ማለቱ ግድ ሆኗል አሁን ላይ ቁሳዊው እንደሌለ ግልጽ ቢሆንም መንፈሳዊው ሀብታችንም ራሱ ድራሹ እንዲጠፋ በከፍተኛ ትጋት እየተሠራበት ነውና ነበረን ማለቱ ይቀላል፡፡ ሊገባኝ ያልቻለው ነገር ግን ከዚህ ማን ምን ዓይነት ትርፍ አንዴት ሆኖ እንደሚያገኝ፤ ጥቅሙ ምን እንደሆነ ነው፡፡ ለሕዝቡ ልጠይቅ የምሻው አንድ ጥያቄ አለኝ  የእናት አባቶቻችን ሀገር ኢትዮጵያ በዓለም  ውስጥ ከነበሩት አራት  ኃያላን መንግሥታት አንደኛዋ  ነበረች፡፡  ይህች ሀገር ዛሬ የዓለም  ጭራ ደሀዋ ሀገር ሆናለች ለምን? ይህ እንዴት ሲሆን ቻለ? እነሱ ጋር የነበረው ጠንካራ ጎን ይህችን ደሀና ደካማዋን ኢትዮጵያ ከፈጠርነው ከእኛ ጋር ያለው ደካማ ጎን ምንድን ነው?
  7. ዕውቅናና መከበርን አትርፎልናል፡- ይህ ድል የማያውቁን አንዲያውቁንና ሀገር ለሀገር ለሚደረግ ግንኙነት ተመራጭ እንድንሆን አድርጓል፡፡ የሚያውቁንም እንዲያከብሩን አድርጓል፡፡ ባጠቃላይ ወዳጅ ብቻ ሳይሆን ጠላትም እንዲሁ በተመሳሳይ ሳይወድ በግድ ዕውቅናና ክብር እንዲሰጥ አድርጎታል፡፡ የዛሬን አያርገውና ከዚያ በኋላ ለመጣችው ኢትዮጵያም ሞገስን አጎናጽፎ በዲንሎማሲው (በአቅንዖተ ግንኙነቱ) ተደማጭ ተከባሪ እንድንሆን አድርጓል፡፡
  8. ለመሪነት ሚና ተመራጭ እንድንሆን አድርጓል፡- ይህ ድል በሰጠን ዕውቅና ሳቢያ በተለያየ አቅጣጫ የፈጠራቸው በቅጭ ግዛት ይማቅቁ የነበሩ ሀገራት የፀረ ቅኝ ግዛት እንቅስቃሴ በሚያደርጉበት ወቅት ይህንን እንቅስቃሴያቸውንና ትግላቸውን እንድንደግፍ እንድናስተባብር ለመጠየቅ አስገድዷቸዋል፡፡ ሀገራችንም ይህንን ትግል የመምራቱን ታሪካዊ ኃላፊነት ሙሉ ለሙሉ በማመን ሀገራቱ ነጻ እስኪወጡ ድረስ የራሷን የጦር መሪዎችንና ተዋጊዎችን በማሰለፍ ጭምር ትግሉን ስታግዝ ስታስተባብር የተጣለባትንም አደራ በሚገባ ተወጥታለች፡፡ ለቀድሞው የአ.አ.ድ ለአሁኑ አ.ህ እና ለሌሎች አህጉራዊና ዓለም ዓቀፋዊ ድርጅቶች መቀመጫነት እንድትመረጥ ያበቃትም የዚሁ ድል ትሩፋት ነው፡፡
  9. ሰንደቅ ዓላማችንን እንድንወስን አብቅቷል፡- በእርግጥ ከአድዋ ድል አስቀድሞም የሀገራችን ነገሥታት ቀይ ቢጫ አረንጓዴ ወይም አረንጓዴ ቢጫ ቀዩን ሰንደቅ ይጠቀሙ እንደነበር ይታወቃል፡፡ ነገር ግን በአዋጅና በይፍ ዕውቅና ተሰጥቶት ሀገራችንንና ሕዝባችንን እንድትወክል የተደረገው ዐፄ ሚኒልክ አድዋ ላይ ይህንን አንጸባራቂ ድል ከገኙ በኋላ እዚያው አድዋ ላይ አዋጅ አስነግረው ከእንግዲህ ወዲህ ይህ ቀይ ቢጫ አረንጓዴ  ሰንደቅ የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ  ሆኗልና ከክብር በላይ ክብርን፣ ከፍቅር በላይ ፍቅርን፣ ከአለኝታነት በላይ አለኝታነትን ስጧት ብለው በማስነገራቸው ይፋዊ ሰንደቃችን ሆና ለመቀጠል ቻለች፡፡

እንግዲህ በአጭር እንቋጨው እንጅ የአድዋን ትሩፋት እንዲህ በቀላሉ ዘርዝሮ የሚጨረስ   ጉዳይ አይደለም፡፡ በመቀጠል የአድዋ ድል ጠላቶች እነማን ናቸው? የሚለውንና ይህንን ቅርስ እንዴት ልንጠብቀው እንችላለን? የሚለውን በአጭር በአጭሩ ዐይተን እንቋጭ ፡፡

የአድዋ ድል ጠላቶች እነማን ናቸው?

የእድለቢስነት ጉዳይ ሆኖ ሀገራችን ኢትዮጵያ ለጠላት የታደለች ሀገር ነች፡፡ በዚህች ሀገር በየትኛውም ሀገር ታይቶ በማይታወቅ መልኩ ለቁጥር የሚያታክቱ ጦርነቶች ከውጭና  ከውስጥ በሚፈጠር ቀውስ ሰበብ አስተናግዳለች፡፡ ይህች ሀገር ካስተናገደችው የጦርነቶች ብዛት አንጻር በታሪኳ በአማካኝ ከ10 ዓመታት ያለፈ የሰላምና የእፎይታ ቆይታ ዓይታ አታውቅም፡፡ ተአምር የሚሆንብኝ ነገር ቢኖር ይህንን ያህል የአውዳሚ ጦርነት ዓይነት ያስተናገደች ሀገር ደብዛዋ አለመጥፋቱ የሥልጣኔና የታሪክ አሻራዎቿም ጥቂቱንም ያህል ቢሆን መቆየት   መቻላቸው ነው፡፡ አሁን ላይ አስቀድሞ የነበሩን ጠላቶቻችንም ሆኑ ሌሎች አዳዲስ ቢኖሩ ጥቃታቸውን እየፈጸሙብን ያለው እንደቀድሞው በወረራ ሳይሆን በመሀከላችን ልዩነቶች እንዲፈጠሩ በማድረግና እርስ በእርስ በማናቆር በማፋጀት ሆኗል፡፡ ይሄም ይዞላቸዋል፡፡ አርቀውና አስፍተው ማሰብ የማይችሉ ወገኖቻችን የሀገራችን የሕዝብ  ለሕዝብ ግንኙነት  ምንም እንኳን እንከን የለሽ ነበር ማለት ባይቻልም በየትኛውም የዓለም ክፍል ከነበረው እጅግ የተሻለው እንጅ ተመሳሳይ እንኳን እነዳልነበረ፤ በበቂ ምክንያትና አማራጭም በመታጣቱ ለሀገር አንድነትና ህልውና ሲባል አንዳንድ የማያስደስቱን ነገሮች መደረጋቸውን መገንዘብ ማስተዋል የተሳናቸው ደናቁርት ለእነኝህ ጠላቶቻችን መሣሪያ በመሆን የሀገራችንንና የሕዝባችንን ህልውና ገደል አፋፍ ላይ አድርሰውታል፡፡ ዛሬ ላይ በየትኛውም የዓለም ክፍል ላይ ያሉ የባርነትና ጭቆና ቀማሽ የነጻነት ደጋፊና አቀንቃኞች የሚኮሩበትን የሚያከብሩትን የሚያደንቁትን  የአድዋን ድልና ያንን ድል ያስገኙልንን አርበኞች እዚህ ኢትዮጵያ ውስጥ ሆነው በጥላቻ የሚመለከቱ መጥፋት መረሳቱን የሚፈልጉ ለዚህም የሚሠሩ ዜጐች ለማየትና ለመስማት ደርሰናል፡፡ መፍትሔው ምንድን ነው ትላላቹ?

ይሄንን ቅርስ እንዴት ልንጠብቀው  እንችላለን?

ይሄንንና  ሌሎች ቅርሶቻችንን ሀብቶቻችንን ታሪኮቻችንን ልንጠብቃቸው  የምንችለው ለነዚህ  ሀብቶቻችን አንድ ዓይነት መግባባት ሲኖረን ሀብቶቹ በሚገባ የመጠበቅ እድል ይኖራቸዋል፡፡ አእምሮ ካለን እዚህ አንድ ዓይነት መግባባት ላይ ላንደርስ የምንችልበት እንድም ምክንያት አይኖርም፡፡ ወደራሳችን ወደ ውስጣችን እንመልከት፡፡ እያደረግነው ያለውን ነገር ከመፈጸሙ በፊት የሚገኘውን ትርፍና ኪሳራ እንመዝን፡፡ እንዲህ እንድናደርግ  እንድንናቆር እንድንባላ የሚመክሩን የሚገፋፉን የሚደግፍን ሀገራት በታሪካቸው ከእኛ የከፋ  የእርስ በእርስ ሰብአዊ መብት ገፈፋ ዝጋብ (record)  ያለባቸው ሀገራት ናቸው፡፡ ነገሥታቶቻቸው ሲያርፉ ጠባቂ እያሉ ሰዎችን ከነነፍሳቸው ግራና ቀኝ ይቀብሩ የነበሩ ናቸው፡፡ የሰው ልጆችን ከአራዊት ጋራ እያታገሉና እያስበሉ ለመዝናኛነት ይጠቀሙ የነበሩ ሀገራት ናቸው፡፡ ይህ ተሞክሮ በሀራችን ፈጽሞ ኖሮ አያውቅም፡፡ ዛሬ ላይ እነሱ እንኳን አንድ ዓይነት መግባባት ደርሰው በአንድነት   ቆመው ለሀገራችው ጥቅሞች በአንድ የተሰለፉ ሆነዋል፡፡ እነሱ ለዚህ የበቁ እንደነዚህ ያሉ ዘግናኝና ኢሰብአዊ ድርጊቶችንና አስተሳሰቦችን ዓይተን የማናውቀው እኛ ኢትዮጵያዊያን እንዴት አንድ ዓይነት መግባባት ላይ ለመድረስ ያቅተናል? ለሀገርና ለሕዝብ እስካሰብን ጊዜ ድረስ ፈጽሞ አያቅተንም፡፡ ሀገርንና ሕዝብን ጠልተንና ንቀን ባንዳነትን ከመረጥን ግን መቸም ጊዜ ቢሆን ልንግባባና የሰላም አየር ልንተነፍስ አንችልም፡፡

ዘለዓለማዊ ክብር ለአርበኞቻችን!!

ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር!!

Zehabesha.com

ይቅርታ መጠየቅ ታላቅነት፣ ይቅር ባይነት ደግሞ ጀግንነት ነው! -በዲ/ን ተረፈ ወርቁ

በመንግሥት ታግዳ ከኅትመት ውጪ የሆነችው ‹‹የአዲስ ጉዳይ መጽሔት›› ዓምደኛ የሆኑት አቶ ሰለሞን ተሰማ ባለፈው ሳምንት በዚሁ በሰንደቅ ጋዜጣ ላይ ባስነበቡን ጽሑፍ የዚሁ ጋዜጣ ም/ዋና  አዘጋጅ አቶ ፋኑኤል ክንፉን፣ አቶ ዳንኤል ብርሃነንና የአዲስ ጉዳይ መጽሔት አንባቢዎችንና ወዳጆችን በይፋ/በአደባባይ ይቅርታ ጠይቀዋል፡፡ አቶ ሰለሞን ባልተረጋገጠ ወሬ በሐሜት የጎዷቸውን በተለይም አቶ ፋኑኤልንና አቶ ዳንኤልን ከታላቅ አክብሮት ጋር በይፋ ይቅርታ መጠየቃቸውን አስነብበውናል፡፡

አቶ ሰለሞን ይህን ማድረጋቸውም አንድም ከእምነታቸው አስተምህሮ፣ ከሕሊና ፍርድ፣ ከሞራል ጥያቄና ለወደፊትም ታሪካችንን ከነትሩፋቱና ከነጠባሳው ለሚወርሱት ልጆቻችን ኩራትና ተምሳሌት ለመሆን በማሰብም ጭምር እንደሆነ በትሕትና ገልጸውልናል፡፡ ይህ በእውነትም ይበል የሚያሰኝ ታላቅ፣ የተቀደሰ በጎና ሰው ከሆነ ሰው የሚጠበቅ ሰናይ ምግባር ነው፡፡

አቶ ሰለሞን ተሰማ ባልተጨበጠ መረጃ፣ በሐሰት ወሬና በሐሜት ላይ ተመርኩዘው በመንግሥት በታገደችው በተወዳጇ አዲስ ጉዳይ መጽሔት ላይ፡-‹‹የአዲስ ዘመን አሮጌ ወሬዎች፣ (ንኩ ጋዜጣ እና ንኩዎቹ ጋዜጠኞች!)›› በሚል ርዕስ ባስነበቡበት ጽሑፋቸው ያስቀየሟቸውን፣ ክብራቸውንና ሰብእናቸውን የጎዷቸውን ሰዎች በይፋ ይቅርታ በመጠየቃቸውም በግሌ ላመሰግናቸው፣ ላከብራቸው እወዳለኹ፡፡

ይህ የእርሳቸው የተቀደሰ፣ መልካምና በጎ ምግባርም በመንግሥት ሥልጣንና ኃላፊነት ባሉ፣ በፖለቲከኞቻችን፣ በአርቲስቶቻችን፣ በታዋቂ ሰዎችና በግለሰቦች ላይ ያለ ምንም ተጨባጭ መረጃና ማስረጃ ስማቸውን፣ ክብራቸውንና ስብእናቸውን በሚነካና በሚያዋርዱ መልኩ የሌሎችን ስም ለሚያብጠለጥሉ፣ ለሚያጎድፉ ሰዎች፣ ሐሜትና አሉባልታን ለሚነዙና ለሚጽፉ መጽሔቶችና ጋዜጦች፣ የመገናኛ ብዙኃን ጥሩ ማሳሰቢያና መልካም ምክርም ጭምር እንደሆነ አስባለሁ፡፡

አቶ ሰለሞን ስሕተታቸውን አምነው በይፋ፣ በአደባባይ ይቅርታ መጠየቃቸው ትልቅነታቸውንና አስተዋይነታቸውን የሚያሳይ ነው፡፡ ይኸው በአብዛኞቻችን ዘንድ እምብዛም ያተለመደው የአቶ ሰለሞን ዕርምጃ ከዕርቅና ከይቅር ባይነት ይልቅ ቂም በቀል፣ ክፋትና ጥላቻ ልክ የባህል ያህል ለነገሠብን ለእኛና ለማኅበረሰባችን ጥሩ የማንቂያ ደወልና ጥሩ ትምህርት ሰጪ ምግባር ይመስለኛል፡፡

ዛሬ፣ ዛሬ በሃይማኖት አባቶችና መንፈሳዊ መሪዎች፣ በመንግሥት ባለ ሥልጣናትና ፖለቲከኞች፣ በአለቆችና የበታች ሠራተኞች፣ በንግድ ሸሪኮችና ወዳጆች፣ በባለ ትዳሮች፣ በቤተሰቦችና በወላጆች መካከልና እንዲሁም በአጠቃላይ በእለት ተእለት ማኅበራዊ ግንኙነቶቻችን ይቅር ባይነት በመብራት የምንፈልገው ውድ ዕንቁ ከሆነብን ሰነባብቷል፡፡ ከይቅርታ፣ ከዕርቅ ይልቅ ቂምኝነት፣ ጥላቻና በቀል የብዙዎቻችን መለያና መታወቂያ ሆኗል፡፡ በርካታዎችም በውስጣቸው ባዘሉትና እሹሩሩ እያሉት ባለው ቂም የተነሳ ውስጣቸው የበቀል እሳት የሚነድባቸው የክፋት፣ የጥፋት መሣሪያ እየሆኑ ነው፡፡

ደመናው ሲዳምን ይወረዛል ገደል፣

ይዘገያል እንጂ መች ይረሳል በደል፡፡

እነርሱ በሬ ሲያርዱ እኛ ጥጃ እንረድ፣

ቢሆንም ባይሆንም እጃችን ደም ይልመድ፡፡

በሚሉ ጥላቻችንና ክፋትን፣ ቂምንና በቀልን በሚሰብኩ፣ በሚያበረታቱና በደም ስራችን ሳይቀር እንዲዋሃዱ የሚያደርጉ ግጥሞችን፣ ሽለላዎችን፣ ቀረርቶዎችንና ፉከራዎችን ሲሰማ ኖሮ፣ ሲሰማ ላደገ ለእንደኛ ዓይነቱ ማኅበረሰብ ይቅርታ መጠየቅ፣ ይቅርታ ማድረግም ሆነ ዕርቅ ብሎ ነገር ጨርሶ የሚታሰብ፣ የሚሞከር ነገር አይደለም፡፡ እናም በአብዛኛው የታሪካችን ገጽ በጥላቻ፣ በእርስ በርስ እልቂትና በመበላላት፣ በቂምና በበቀል፣ በደም የተዥጎረጎረ፣ የደመቀ ነው፡፡

ስለሆነም ይቅርታን የሚሰብኩ፣ የሰላምና የዕርቅ ሰዎችን ታላቅና ጀግና የሚያደርግ ባህላችን እጅጉን የደበዘዘ ነው፡፡ ከዛ ይልቅ በአብዛኛው ቂምን በልቡ አርግዞ የወፈጀውን ያህል ጊዜ ፈጅቶም ቢሆን አድብቶና ጠብቆ ሌላውን የሚበቀለውን፣ የትናንትና በደልንና ጥፋትን በደም ካሣ የሚያወራርደውን ሰው ጀግና ብሎ ለመሾምና ለመሸለም የሚተጋና የሚያተጋ ባህልና ታሪክ ነው ያለን፡፡

ግና ይቅርታ መጠየቅም ሆነ ይቅርታ ማድረግ ታላቅነት፣ ጀግንነት ነው፡፡ አቶ ሰለሞን ይህን ለብዙዎቻችን ተራራ የመውጣት ያህል የሚከብደንን ይቅርታ የመጠየቅን ጉዳይ በአደባባይ ለማድረግ በመፍቃደቸው ሊመሰገኑ ሊከበሩ ይገባቸዋል፡፡ በመሠረቱም የትኛውም የዓለማችን ሃይማኖቶች ትእዛዝና አስተምህሮም ኾነ በዓለማዊው ወይም በዘመናዊው ዓለም ዕውቀት ይቅር ባይነት/ይቅርታ ማድረግ ቅዱስና በእጅጉ የሚበረታታ መልካም ነገር እንደኾነ ነው አስረግጠው የሚነግሩን፡፡

ታላላቅ በሆኑት በክርስትናም ኾነ በእስልምና ሃይማኖቶች አስተምህሮ ዘንድም ይቅር ባይነት፡- አፍቃሪ፣ ቸር፣ ርኁርኁርና አዛኝ ከኾነው ከፈጣሪ ዘንድ ከተቀበልነው ገደብ የለሽ ይቅርታና ምሕረት ለሌሎችም ወዳጅና ጠላት ሳንልና ሳንለይ፣ ሳንሰስት የምናካፍለውና የምንከፍለው የፍቅር ዕዳችን እንደኾነ ነው አብዝተው፣ አስፍተውና አምልተው የሚናገሩት፣ የሚያስተምሩት፡፡

ከሃይማኖታዊ አስተምህሮ ባሻገርም በጤና ሳይንስና እና በሥነ ልቦና ጥናት ረገድም ይቅር ባይነት ከፍተኛ ጠቀሜታ እንዳለው ያመለክታሉ፡፡ የባለሙያዎች ጥናቶች እንደሚያሳዩትም ነገሮችን በይቅርታ ማለፍ መቻል የዕለት ተዕለት ማኅበራዊ ግንኑነታችንን ጤናማና ሚዛናዊ እንዲሆን ከማድረግም ባሻገር ከተለያዩ የጤና እክሎችና በሽታዎች እንደሚታደገንና፣ እንዲሁም ሕይወትን በፍቅርና በተስፋ፣ በደስታና በሰላም ለመኖር የሚያስችለንን ኃይል በሕይወታችን እንደሚጨምርልን ያስረዳሉ፡፡

ጄኒ ሴፈር የተባሉ ምሁር What We Forget about Forgiveness በሚል ርዕስ ‹‹ሳይኮሎጂ ቱዴይ›› መጽሔት ላይ በ2014 እትም ላይ ይቅርታን በተመለከ ባስነበቡት ጥናታዊ ጽሑፋቸው በአሜሪካና በአውሮፓ አገራት ካለፉት ዐሥር ወይም ዐሥራ አምስት ዓመታት ጀምሮ የይቅርታ ጉዳይ ከግለሰብ ጀምሮ እስከ ፖለቲከኞች ድረስ ዐቢይ የመነጋገሪያ አጀንዳ መሆኑን ጠቅሰው ጽፈዋል፡፡

ሴፈር በዚህ ጹሑፋቸው በአሜሪካንም ሆነ በተለያዩ የአውሮፓ አገራት በሚገኙ ታላላቅ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማትና ዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ የይቅርታ/የዕርቅ የጥናትና የምርምር ማዕከሎችን በስፋት ማቋቋማቸውን ያትታሉ፡፡ እኚህ ምሁር በአሜሪካ አገር በዊስኮንሲን ሜዲሰን ዩኒቨርሲቲና የስታንፎርድ ዓለም አቀፍ የይቅርታ/የዕርቅ ፕሮጀክት፣ በሕክምና ሳይንስ፣ በሥነ-አእምሮ፣ በሥነ-ልቦና እና በማኅበረሰብ ሳይንስ ጥናቶች ረገድ እየወጡ ያሉ ጥናቶች ጠቅሰው እንዳስነበቡት፡-

የሌሎችን በደል ይቅር የሚሉ፣ ይቅርታ ለመስጠትም ሆነ ለመቀበል ፈቃደኛ የሆኑ ሰዎች የተሻለና ጤናማ ሊባል የሚችል ማኅበራዊ ግንኙነት እንዳላቸውና አካላዊና አእምሮአዊ ጤንነታቸው መልካም እንደሚሆን አስነብበዋል፡፡ በተቃራኒው ሆነ ብለውም ሆነ ሳያውቁ ሌሎች ሰዎች ባደረጉባቸው በደል የተነሳ የሚብሰለሰሉ፣ በውስጣቸው ቂም የሚይዙና ለመበቀል ምቹ ጊዜን የሚጠባበቁ፣ ይቅርታ ለመጠይቅም ሆነ ይቅርታ ለማድረግ ፈቃደኛ ያልሆኑ ሰዎች በአብዛኛው ለድብርት፣ ለጭንቀት፣ ለደም ግፊት፣ ከፍተኛ ለሆነ ሥነ ልቦናዊ ቀውስና የጤና እክል እንደሚዳረጉ ጨምረው አስነብበዋል፡፡

ሴፈር በዚህ ጽሑፋቸው የይቅርታና የዕርቅ ፕሮጀክቶች የዘር ማጥፋት ዘመቻ፣ እርስ በርስ ጦርነት፣ ግጭትና እልቂት በተካሄደባቸው እንደ ሩዋንዳ፣ ብሩንዲ፣ ሴራሊዮን፣ ካምቦዲያ፣ ደቡብ አፍሪካ ባሉ አገራትም ተጨባጭ የሆነ ለውጥ ማምጣታቸውን አትተው ጽፈዋል፡፡

በተለይ በአፓርታይድ አገዛዝ ወቅት በደቡብ አፍሪካ ለደረሰው ዘግናኝ የሆነ ኢሰብአዊ ድርጊት፣ የዘር ማጥፋት ዘመቻ፣ ጭፍጨፋ፣ ግድያና ሥቃይ በይቅርታ ጀግናው በማንዴላና በአቡነ ዴዝሞን ቱቱ መሪነት በደቡብ አፍሪካ የተቋቋመው South African Truth and Reconciliation Commissionበሚሊዮን የሚቆጠሩ ቂምን ያረገዙ ደቡብ አፍሪካውያን የበቀልና የእልቂት ሰይፍ ወደ ሰገባው እንዲመለስ በማድረግ በቋፍ ላይ የነበረችውንና በጥፋት መንገድ የቆመችውን ያችን አገር ወደ ሰላምና ዕርቅ መንገድ በማምጣት ታላቅ የሆነ ታሪካዊ ሚናን መጫወታቸውን ሁላችንም አንዘነጋውም፡፡

በመጨረሻም በእርግጥም ይቅርታ መጠየቅም ሆነ ይቅርታ ማድረግ በቁሳዊውም/በዘመናዊው ሆነ በመንፈሳዊው ዓለምም እጅግ ታላቅና የተወደደ ቅዱስ ምግባር መሆኑን ላሰምርበት እወዳለኹ፡፡ ታላቁ ቅዱስ መጽሐፍም፡- ‹‹እርስ በርሳችሁ ይቅር ተባባሉ፡፡ የወንድሞቻችሁን ኃጢአት ይቅር ብትሉ የሰማዩ አባታችሁም የእናንተን በደል ይቅር ይላችኋል፡፡›› ‹‹መባህን ከማቅረብህ በፊት አስቀድመህ ከወንድምህ ጋር ታረቅ›› ሲል ይናገራል፡፡ የክርስትና ሃይማኖት ጸንቶ ከቆመባቸው ታላላቅ ዓምዶችም መካከልም ፍቅር፣ ምሕረትና ይቅርታ ዋንኞቹ ናቸው፡፡ ፈጣሪ አምላክም ከፍጡሩ ወይም ከሰው ልጆች ጋር ያለው ግንኙነትም ፍቅርን፣ ምሕረትንና ይቅርታን የተሞላ ወይም መሠረት ያደረገ ነው፡፡

ስለሆነም እኛ የሰው ልጆች ከፈጣሪ ጋር ሊኖረን የሚገባው ግንኙነት የሚወሰነውም ከሌሎች ሰዎች ጋር ባለን የፍቅር ግንኙነት ነው፡፡ ይህ ፍቅር ደግሞ የሚታገሥ፣ የሌሎችን በደል ማይቆጥር፣ ይቅር ባይ፣ ታጋሽና እውነተኛ ነው፡፡ ሌሎችን ስንወድ፣ ከልብ ስናፈቅር የዛሬ በደላቸውን፣ ስሕተታቸውን  ሳይሆን የትናትና መልካምነታቸውና ወዳጅነታቸው ትዝ እያለን በደላቸውን ሳንቆጥር ይቅር እያልናቸውና እያፈቀርናቸው አብረናቸው በይቅርታ ለመኖር የሚያስችለንን ኃይል፣ ጉልበትና ጸጋ እናገኛለን፡፡

ትናንትና በሆነው የመበላላት፣ እርስ በርስ እልቂት አስቀያሚ የሕዝባችን ታሪክ የተነሣ፣ በዘርና በቋንቋ ተከፋፍለው በጎሪጥ ለሚተያዩ፣ ሊፈርሱ አንድ ሐሙስ የቀራቸውን በቋፍ ላይ ያሉ ትዳሮችን፣ ሊበተኑ ያሉ ልጆችን፣ በበደልና በቂም የደፈረሱ፣ የተበላሹ የፍቅር ወዳጅነቶችን፣ ቤተሰባዊና ማኅበራዊ ግንኙነቶቻችንን ለመታደግ ይቅርታ፣ ሰላም፣ ዕርቅን ማውረድ ዋንኛውና ብቸኛው መፍትሔ ነው፡፡

አበው ‹‹ከታረቁ አይቀር ከልብ፣ ከታጠቡ አይቀር እስከ ክንድ››፣ ‹‹ቂም ይዞ ጸሎት ሳል ይዞ ስርቆት›› እንዲሉ በዚህ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤ/ን ኦርቶዶክሳውያን አባቶች፣ አገልጋዮችና ምእመናን እየጾምነው ባለነው በዚህ በታላቁ በዐቢይ ጾምም ቂምን ትቶ፣ ይቅርታ መጠየቅም ሆነ ከልብ የሆነ ይቅርታ ማድረግ ጾማችንን ተቀባይነት ያለውና ታላቅ የሆነ መንፈሳዊ ብድራት ወይም ዋጋ የሚያስገኝንልን ቅዱስ ተግባር እንደሆነ ማስታወስ እፈልጋለኹ፡፡

በተጨማሪም አላስፈላጊ ከሆኑ የጤና እክሎች ድብርት፣ ጭንቀት፣ የደም ግፊት፣ ከማይፈለጉ ሥነ ልቦናዊ ቀውሶችና ውጥረቶችም ለመዳንም ይቅርታ ማድረግምም ሆነ ይቅርታ መጠየቅ መፍትሔ መሆኑን ሁላችንም ልብ ልንል ይገባናል፡፡ ይቅርታ መጠየቅ ታላቅነት/ትልቅነት፣ ይቅር ባይነት ደግሞ ጀግንነት ነውና!! ለሕዝበ ክርስቲያን በሙሉ የፍቅርና የይቅርታ የጾም ወራት እንዲሆን በመመኘት ልሰናበት!!

ዲሞክራሲ ለኢትዮጵያ እጣ ክፍሏ አይደለም ይሆን?

ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊነትን በትክክል የማይተረጉም ወይም የማይገልፅ እና የአለምን ነባራዊ ሁኔታ ከማንነቱ አንፃር ማየት የማይችል ህዝብ ለራሱ የሚጠቅመውን ገንቢ የሆነ ተግባራትን ሊፈፅም አይችልም፡ ምክንያቱም የስነ ልቦና ባርነት ያድርበታልና፡፡

በ1960ዎቹ መጀመሪያ በኢትዮጵያ ውስጥ ለውጥ ለማምጣት የታገለው ትውልድ ቆራጥ ትውልድ ነበር፡፡ ነገር ግን መብትን ማስከበር፣ ነፃነትን መጎናፀፍ፣ ብልፅግና ማስፈን ወዘተ የሚል መርሆዎችን ይዞ ይነሳ እንጂ የተመኛቸውን እነዚህን ለውጦች ለማምጣት የሚያስችል የእውቀት የባህልና የስብእና ብቃት አለኝ ብሎ በጥሞና ራሱን አለመመርመሩ ነበር ችግሩ፡፡ በዚያ ዘመን ለውጥን አመጣለሁ ብሎ ለትግል የተነሳው ኢትዮጵያዊ ምሁር የነፃ አውጪነት ሚና ሲጫወት ለዚህ የሚመጥን ብቃት እንዳለው በሚገባ አላሰበበትም::

ሀገራዊ ታሪካችንንም ሆነ ፖለቲካዊ እውነታዎችን በግልፅ ፍርጥርጥ አድርገን የመናገር ችግር አለብን፡፡ አንድን የፖለቲካ ሁኔታ ወደኋላ መለስ ብለን አንስተን ስንወያይ እውነታውን ለመቀበል ምን ያህል ዝግጁ ነን የሚለው መታየት ያለበት ይመስለኛል፡፡ እኔ መሰረታዊ ችግር ነው የምለው ይህንን ነው፡፡ በምድረ ኢትዮጵያ ስለዲሞክራሲ ሲነገር፣ ሲደሶከር፣ ሲዘመርና ሲተነተን ከአራት አስርት አመታት በላይ መቆጠሩ እውነት ነው፡፡ ነገር ግን የተነገረውንና የታወቀውን ያህል የዲሞክራሲ ዘር ተዘርቶ ፍሬ ሲያፈራ አልታየም፡፡ ወይም ሊታይ አልቻለም፡፡ የዲሞክራሲ መርህ የተቀበሉ አብዛኛው የአለም ሐገራት ወደላቀ እድገት ብልጽግና እና የተሟላ ሰላም ተሸጋግረው ብሔራዊ እና ሀገራዊ ልእልናቸውን ለተምሳሌትነት ባበቁበት ዘመን እኛ ኢትዮጵያውያን ለዲሞክራሲ ባይተዋር ሆነን መገኘታችን የአደባባይ ሚስጥር ነው፡፡ በዚህ የተነሳ ስለዲሞክራሲ እያነበብን የምንብከነከንበት፣ ዲሞክራሲን ለማለም እንጂ ለመኖር ያልታደልን ህዝብ ለመሆን ተገደናል፡፡ በአጭሩ የዲሞክራሲ ፅንሰ ሀሳብ ለእኛ ለኢትዮጵያውያን እርስ በእርስ የምንጠላለፍበት፣ ተጠላልፈንም የምንወድቅበት ሆኗል ብንል ስህተት አይሆንም፡፡

በዲሞክራሲ ሰበብ ኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን ከአርባ አመታት በላይ በተዘፈቅንበት ችግር ለቁጥር የሚታክቱ በርካታ ምክንያቶችን መዘርዘር እንችላለን፡፡ ከነዚህ በርካታ ችግሮች መሀል ዋናው የዲሞክራሲ ፅንሰ ሃሳብ በቀደምትነት እያቀነቀነ ለለውጥ የተነሳው ትውልድ (1960ዎቹ) ህይወት ተቀጥፏል፣ ሰበቡ ባመጣው ጦስ ምክንያት ምትክ የማይገኝላቸው ወጣቶች አገራቸውን ለቀው ለመሰደድ ተገደዋል፡፡ በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ወገኖችም ለሞት እና ለእስር ተዳርገዋል፤ አካላቸው መንፈሳቸውም እንዲኮላሽ ሆኗል፣ ቤተሰብ ተበትኗል….ወዘተ፡፡ በዚህም የተነሳ በአብዛኛው የኢትዮጵያ ህዝብ ህሊና ውስጥ የማይሽር ቁስል እንደማህተም ተቀርጾ ሊኖር ግድ ሆኗል፡፡ ትውልዱ በዲሞክራሲ ስም የደረሰበት ግፍና በደል ሁሉ አንገት ደፊ ሆኖ ለመኖር እስከመወሰን ደርሶ እንደነበር የቅርብ ጊዜ ትዝታችን ነው፡፡ እንዲህም ይሁን እንዲያ የዲሞክራሲን ስርዓት ለዚች ሀገር ለማስፈን የታገሉና የሚታገሉ አልጠፉም ፡፡ ግን ምን ያደርጋል? በየዘመናቱ ለሀገራዊ ራዕይ የተዋጣለት ስኬት ያስገኛል የተባለው ዲሞክራሲ ከተራ ቃልነት በዘለለ ይህ ነው የሚባል ውጤት ሳያስገኝ ይኸው እንዳለን አለን፡፡ ለምን?

እኛ ኢትዮጵያውን የዲሞክራሲ ፅንሰ ሃሳብ ስላልገባን? ወይስ ሊገባን የማይችል ስለሆነ? ወይም የዲሞክራሲን መሰረታዊ ሃቆች በቃል ብቻ የምናነበንበው ሌሎች ያሉትን እንደበቀቀን ደግመን የመናገር ልማድ ስለተፀናወተን? ወይስ ሌላ ያላየነውና ያልለየነው ምክንያት ይኖር ይሆን?… ወዘተ ብለን መጠየቅና ራሳችንን መመርመር ግድ የሚለን ይመስለኛል፡፡

በኢትዮጵያችን ለዘመናት የናፈቅነው ዲሞክራሲ እውን ሆኖ ህዝቦችዋ በሰላም እና በመተሳሰብ በጋራ አብረን እንኖር ዘንድ መልካም ምኞቴ ነዉ፡፡

dagnachew-tegegn.fw

ለዲያቆን ዳንኤል ክብረት ፣ከኤርሚያስ ለገሰ /የመለስ ትሩፋቶች /የተሰጠ ምላሽ

Ermiasከአንድ ሰአት በላይ የፈጀውን ጥናታዊ ጵሁፍህን ሰማሁት። ሰምቼ ስጨርስ ደነገጥኩ። ከራሴም ጋር ለሰአታት ሙግት ገጠምኩ ። ኢህአዴግን ለቅቄ የወጣሁት ልቤ የፈቀደውን በነጳነት ለመናገር ነውና የማውቀውን እና የሚሰማኝን መናገር እንዳለብኝ ተሰማኝ ። ርግጥ በሐይማኖት ጉዳዬች ላይ መናገር ከባድ እንደሆነና ዋጋ እንደሚያስከፍል ጠንቅቄ አውቃለሁ ። በሌላ በኩል የሚያውቁትን አለመግለጵም የፀፀት ዋጋ አለው። በመሆኑም ባለመናገሬ ከሚሰማኝ ሙግት መናገሩን ስለመረጥኩ የሚከተለውን አጭር አስተያየት ለመስጠት ተገደድኩ።
1• ያቀረብከውን መረጃዎች እንዴት እንዳሰባሰብካቸው የተገለፀ ነገር የለም። በተለይም በድህረና ቅድመ ምርጫ 97 ባሉት ሶስት አመታት( ከኃላም ከፊትም) ያቀረብካቸውን መረጃዎች ምንጭ ማወቅ እፈልጋለሁ ። ይህን ጥያቄ የማነሳበት መሰረታዊ ምክንያቶች ስላሉኝ ነው።

1•1• በኢትዮጵያ አቆጣጠር 2001 አ• ም• ኢሕአዴግ ለሕዝቡ ይዞለት የመጣው እቅድ ” በአክራሪነት ” ስም ሀይማኖቶችን ማዳከም ነበር። ይህንንም ለማቀጣጠል እንዲረዳው በኢህአዴግ ቢሮ፣ በኮሙዩኒኬሽን ጵ/ ቤት፣ ፌደራል ጉዳዬች እና ፌደራል ፓሊስ መረጃ እንዲሰባሰቡ ተደረገ። የእስልምና ጉዳዬች ላይ ዝርዝር ጥናቱን እንዲሰራ የቤትስራ የተሰጠው ሽመልስ ከማል ነበር። ዛሬ አንተ ካቀረብክልን ውስጥ ግማሹ የቃላት ለውጥ እንኳን ሳይደረግለት በሽመልስ ከማል ጥናታዊ ፅሁፍ የቀረበ ነበር። በወቅቱ እጅግ ከመደንገጤ የተነሳ ሽመልስ እንዴት እንዲህ አይነት ጥናት እንደሰራ ለማወቅ ከጀርባው መጓዝ ነበረብኝ ። መጓዜ ያልጠበኩትን ውጤት አመጣ። ሽመልስ በእስልምና ላይ ከፍተኛ ጥላቻ የያዘው በቤተሰቡ ውስጥ በተፈጠረው ምስቅልቅል እድገት መሆኑን ተገነዘብኩ። አባቱ በአንድ ወቅት የመስኪድ አስተዳደር ነበሩ። በኃላ የሳውዲ ጉዞ አድርገው ሲመለሱ አስተዳደሩን በመነጠቃቸው ከሀይማኖቱ በተቃራኒ ተሰለፋ ። ” ከመካ መዲና ደርሶ መልስ” የሚል መጵሀፍ አሳትመው ክርስትና ተነሱ። ስማቸውም ወደ ሀይለየሱስ ተቀየረ። ባስታወቀው እርምጃ ቤታቸው ተመሰቃቀለ።ወንድማማች እና እህታማቾች የሚጠሩበት የአባት ስም እስከ መለያየት ደረሰ። ባጭሩ የሽመልስ ፀረ -እስላም የመሆን ምንጩ ይሄ ነው። በመሆኑም በሽመልስ ሲቀርቡ የነበሩ ዳታዎችና ትንታኔዎች እንደወረዱ ከአንተ ሲቀርቡ ስሰማ የመረጃ ምንጭህን ተጠራጠርኩ። በተለይ ቴኳንዶ ፣አክሱም፣ መያዶች …ወዘተ ብለህ የገለጵከው የካርቦን ግልባጭ ሆኖ አግኝቸዋለሁ።

1•2• ሌላኛው ዳታ የሰበሰበው የፌደራል ጉዳዬች ሚኒስተር የነበረው ዶክተር ሽፈራው ከፓሊስ ጋር በመሆን ነበር። ዶክተሩ ያጠናቀረው መረጃ ተመሳሳይ ሲሆን በማጠቃለያው ” የኦርቶዶክስ አክራሪነት አለ” የሚል ነበር። የአክራሪነቱ አስኳል ማህበረ ቅዱሳን እንደሆነ አፅንኦት ሰጥቶበት ነበር። ይህ የዶክተሩ መረጃ በአንተ ጥናታዊ ፅሁፍ ላይ አልቀረበም ።
( ግምቴን አስቀምጬ ለማለፍ ይህን የዶክተር ሽፈራው ዳታና ትንታኔ ለሌላ የእስልምና መምህር እንዲደርሰው ይደረግና እንደአንተ እንዲያቀርብ ይደረጋል ። ርዕሱንም ” የኦርቶዶክስ አክራሪነት ” ብሎ እንዲጠራው ይደረጋል ።)

2• የመረጃዎቹ ምንጭ እንደተጠበቀ ሆኖ ኩነቶቹ ሲፈጠሩ ሀገሪቷ የነበረችበትን ፓለቲካዊ ሁኔታ ከግምት አላስገባህም። ለምሳሌ ከምርጫ 97 በኃላ በኦሮሚያ የተከሰቱት የሐይማኖት ግጭቶች የተጠነሰሱት በአቶ መለስና ደህንነት ጵ/ ቤት ሲሆን ዋነኛ አሰፈጳሚዎቹ እነ አባዱላና የኦህዴድ ካድሬዎች ነበሩ። ” ቅንጅት የክርስቲያን ጠበቃ ነው” የሚለው መልእክት የተቀረፀው አንተ በጥናታዊ ጵሁፍህ ላይ ” ውሸት ሲደጋገም እውነት ይሆናል” የሚለው መርሆ አቀንቃኝ የሆነው አቶ በረከት ነው። በየጉራንጉሩ መልእክቱን ያሰራጩት ደግሞ ” እኔ ከሞትኩ… ” በሚለው ብሂል እነ አባዱላና ጁነዲን ናቸው። በተለይ በድሬደዋ የጠነሰሱት ሴራ ባይከሽፍ ኖሮ ዘግናኝ እልቂት ይከሰት ነበር። በመሆኑም ከምርጫ 97 በኃላ የተከሰቱት ግጭቶች ( በተለይ በኦሮሚያ) ጠንሳሾቹ አሁን እየመሩን ያሉት ፓለቲከኞች ሲሆኑ መንስኤውም ፓለቲካው የፈጠረው ነበር። አንተ ግን በየትኛው ቦታ ላይ የፓለቲከኞቹን ሚና ማንሳት አልፈለክም ። ይልቁንስ መንግስት አበረደው፣ መከላከያ አረገበው ማለትን መርጠሀል። ጥናትህን ሰፋ ብታደርገው ኢትየጵያ ውስጥ አክራሪነት በዋነኛነት እየሰፋ የሄደው በፓለቲካው መበላሸት ምክንያት የተፈጠረ መሆኑን ትደርስበት ነበር። አሁንማ በድጋሚ ለማየት ጊዜው አልረፈደም።

3• በጥናታዊ ጵሁፍህ ላይ በአሁን ሰአት ያለውን የኢትየጵያ ሙስሊሞች ” ኢትዬጲያዊነት የተላበሰ፣ ሰላማዊና ፍትሐዊ ጥያቄ” ማንሳት አልፈለክም ። እንደሚታወቀው የኢትዮጵያ ሙስሊሞች የተቃወሙት የመንግስት ጣልቃ ገብነት ነው።ኢህአዴግ ከሀይማኖቱ ላይ እጁን እንዲያነሳ ነው በሰላማዊ መንገድ እየጠየቁ ያሉት። አመራራችን በእኛ ይመረጡ፣ ተቋማችንን ራሳችን እናስተዳድር የሚል ነው። ለዚህ ደግሞ እኔ በየትኛውም ቦታና ሰአት ምስክር መሆን እችላለሁ። ታዲያ አክራሪን፣ አክራሪ ካልሆነው ለይቶ የማስረዳት አላማ ካነገብክ ለምን ፍትሐዊ የሆነውን ይህን ጥያቄ ሳታነሳ ቀረህ? እንደ ገዥዎቻችን ” የሙስሊሙ ጥያቄ አክራሪነት የወለደው ነው” የምትለን ከሆነም ወደ መድረክ አውጣውና እንነጋገርበት ።

4• አጀንዳህ ስለ ” ሙስሊም አክራሪነት ” ሆኖ ወደ ማጠቃለያህ ላይ በውጭ ሀገር ያለውን ሲኖዶስ ወደ መዝለፍ ለምን ተሸጋገርክ። ከአንደበትህ የወጣው ቃል ” የሐሰት ሲኖዶስ ተቋቁሞ መንጋ የማይጠብቅ ጳጳሳት ይሾማል ” የሚል ነው። ይህ ንግግር በራሱ አንድነት የሚያመጣ ነው? ውጭ ያለው ሲኖዶስ የሐሰት ነው / አይደለም ከሚለው ትርክት በፊት ይህ እንዲፈጠር ያደረገው ምክንያት ምንድነው የሚለውን ብታነሳ የተሻለ መልስ ታገኝ እንደነበር እገምታለሁ። ሐገር ቤት ያለውን ሲኖዶስ ማን ከጀርባ ሆኖ እንደሚያሽከረክረው ካላወክ በኢትዮጵያ ምህዳር ላይ መኖርህን እንድጠራጠር ያደርገኛል።

4• ሌላኛው ” ለምን አሁን?፣ ምን አዲስ ነገር አለ?” የሚል ጥያቄ እንዳነሳ አድርጐኛል ። የሙስሊሞች ሰላማዊ ትግል በተጠናከረበት፣ መንግስት በጅምላ ማሰር በጀመረበት ፣ ማህበረ ቅዱሳን ላይ በተዛተበት ወቅት ለምን የሚከፋፍል አጀንዳ ይዞ ብቅ ማለት ተፈለገ? የማን አጀንዳ ነው እየተራመደ ያለው የሚለውን ማየት ተገቢ ይሆናል
Ermias Legess / የ መለስ ትሩፋቶች/

– See more at: http://satenaw.com/amharic/archives/4934#sthash.8DKplUCJ.dpuf

ከአንድነት ሰሜን አሜሪካ ድጋፍ ማህበርና ከሰማያዊ ሰሜን አሜሪካ ድጋፍ ማህበር የተሰጠ የጋራ መግለጫ!!

እንደሚታወቀው የኢህአዴግ አገዛዝ ከጊዜ ወደ ጊዜ ጸረ ዲሞክራሲ አካሄዱ እየባሰበት የመጣና መሠረታዊ መብቶችን ሙሉ በሙሉ ሊባል በሚችል መልኩ ማፈኑን አጠናክሮ ቀጥሎበታል፡፡ በቅርቡ በአንድነትና በመኢአድ ፓርቲ ላይ አገዛዙ በሚያዝዛቸው የተቋማት ኃላፊዎች ቀጭን ትዕዛዝ የፓርቲዎቹ ሕልውና ለጥቂት ግለሰቦች ተላልፎ ተሰጥቷል፡፡ ይህ ዓይነቱ ህገ-ወጥ ድርጊት መቼዉም ቢሆን ተቀባይነት አይኖረውም! ለአገራችን የሠላማዊ የስልጣን ሽግግር ከባድ መሠናክል ሊሆን እንደሚችል ሁሉም ይገነዘባል ብለን እናምናለን፡፡ የኢህአዴግ የምርጫ ቦርድ እንዲህ ዓይነቱን ክፉ ስራ ሲወስን የአገራችንን የረጅም ሠላም አይተው ሣይሆን በአገዛዙ ቁንጮ ሰዎች በመታዘዝ በተቋም ስም የሚሠሩት የማደናገር የድንቁርና ተግባራቸዉ አንድ አካል ነው ብለን እናምናለን፡፡ ማህበራችን ይህን ድርጊት እጅጉን ያወግዛል። በመሆኑም ድርጊቱን በጋራ እንቃወማለን።

በምርጫ ቦርድ ስም የተወሰነው ህገ-ወጥ ውሣኔ ምክንያት መላ የአንድነትና የመኢአድ አባላት የፖለቲካ እንቅስቃሴአቸው ተገድቧል፡፡ ይሁን እንጂ ለአገራቸው ካላቸው ፅኑ ፍቅር አኳያ ትግሉን ለማስቀጠል ከሠማያዊ ፓርቲ ጋር አብሮ ለመሥራት የአባልነት ፎርም በመሙላት ትግሉን ቀጥለዋል፡፡ ይህ ዓይነቱ የአባላት ቆራጥ ውሣኔ ሊበረታታና ሞራል ሊሰጠው የሚገባ ነው ብለን እናምናለን! እኛም በሰሜን አሜሪካ የምንገኝ የሁለቱ የድጋፍ ማህበራት ሙሉ በሙሉ ድጋፋችንን እንደምንሰጥ እናረጋግጣለን፡፡

ስለሆነም በሰሜን አሜሪካ የምንገኝ የአንድነትና የሠማያዊ የድጋፍ ማህበራት በጋራ በኮሜቴ ደረጃ ተዋቅረን በዋና ዋና ጉዳዬች ላይ ማለትም በፋይናንስ፤ በእስረኞች ጉዳይ እና በዲኘሎማሲው ዙሪያ ሙሉ በሙሉ በትብብር አብረን እየሠራን የሰማያዊ ፓርቲንና ሌሎች በሃገር ውስጥ የሚንቀሳቀሱ ሃይሎችን በጋራ ድጋፍ ለመስጠት ውሣኔ አሣልፈናል፡፡ በቀጣይም በጋራ የኮሚቴ ውይይቶችን እያደረግን ለሰማያዊ ፓርቲ የሚያስፈልጉ የሞራልና የማቴሪያል ርዳታ እንደምንሰጥ እናረጋግጣለን፡፡
የሰማያዊና የአንድነት ሰሜን አሜሪካ ድጋፍ ማህበራት
የካቲት 19 2007 ዓ/ምANAASO-Blue

አጥፍቶ ጠፊዎች! – ከኪዳኔ አማነ

በአሁኑ ወቅት አገራችን ኢትዮጵያ እጅግ ጥንቃቄ በሚያስፈልገው ጊዜ ትገኛለች፡፡ ሃላፊነት እሚሰማው ተቃዋሚ ፓርቲ እና ለህግ ተገዢ የሆነ ጥበበኛ ገዚ ፓርቲ ትሻለች፡፡ ዛሬ ኢትዮጵያ በብሄር ፍትጫ የተወጠረች እና ልትበጠስ ትንሽ የቀራት ስስ ክር ሆናለች፡፡ አገሪትዋ በአንድ በኩል ኢህኣዴግ እሚባል ላፀደቀው ህግ ደንታ የሌለው ጠበንጃ አምላኪ ጉጅሌ ስትታመስ በሌላ በኩል ደግሞ ኢህኣዴግን በማንኛውም መንገድ ከስልጣን ለማውረድ ብቻ እንጂ ስለነገይትዋ ኢትዮጵያ ግምት ውስጥ አስገብተው የማይንቀሳቀሱ አንዳንድ ተቃዋሚዎች በመኖራቸው የወደፊት ተስፋዋ እየጨለመ ነው፡፡ እነደኔ እነደኔ እነዚህ ሁለቱም አካላት ለአገር የማይጠቅሙ አጥፍቶ ጠፊዎች ናቸው፡፡ ሁለቱም አጥፍቶ ጠፊዎች አጀንዳቸው ስልጣን እንጂ ኢትዮጵያና ህዝብዋ አይደለም የሚያስቀድሙት፡፡ፋሺስት ደርግ ስለዴሞክራሲ ሁሌ ይናገር እነደነበረና በዴሞክራሲ ስም ምሎ ሲገዘት እንደነበረ ሁሉ የአሁኑ ገዢው ሃይልም ከዴሞክራሲ ሆድና ጀርባ ሆኖ ስለ ዴሞክራሲ ይዘምራል ፅንፈኛ ተቃዋሚዎቹ ደግሞ ከጠላቶቻችን ጋር አብሮው ስለ አገር እንደሚጨነቁ ይለፍፋሉ፡፡ ይሄ አጥፍቶ ጠፊነት አይደለምን? እንዲሁም ኢህኣዴግ ከስልጣን ላለመውረድ የቻለዉን ሁሉ በውንብድና ይጨፈልቃል ሃላፊነት የማይሰማቸው ጫፍ የረገጡ አክራሪ ተቃዋሚዎች ደግሞ ስርዓቱና አገሪትዋ አናግተው ስልጣን ላይ ቁጢጥ ለማለት ሌት ተቀን ይፍጨረጨራሉ፡፡ አንዳንዶቹ እብድ ተቃዋሚዎችማ (ባህር ማዶ የሚገኙ)ህዝብና ድርጅት መለየት አቅቷቸው ሁሉም ህዝብ በትግራይ ህዝብ ላይ ጭፍጨፋ እንዲያካሂድ የሚሰብኩ አሉ(አንድ ብሄር ከምድረገፅ አስወግደው የኢትዮጵያ ችግሮች ሁሉ ብን ብለው በአንዴ ይጠፉ ይመስል )፡፡
እነዚህ ከጠላቶቻችን (ከነሸዓብያ) በማበር አገራችን ለመውጋት ሁላ እየተንቀሳቀሱ እንደሆኑ በዛ አውዳሚ ሚድያቸው ይነግሩናል፡፡ ይሄ (ከጠላት ጋር ማበር) የፀጥታና የአገር ጉዳይ ስለሆነ (ገዢው ፓርቲ ብቻ የሚመለከት ብቻ ስላልሆነ) የሰለጠነ አቀዋም ልንይዝ ይገባል፡፡ በብሄራዊ ጥቅም እና ደኅንነት አንድና ተመሳሳይ ሃሳብ ማንፀበረቅ አለብን፡፡ የሚከተሉትን የትግል ስልት አዋጭ ነው ብለው ካመኑ ከኢትዮጵያ ህዝብ ጋር ሆኖው በኢትዮጵያ መሬት ላይ መፋለም ነበር እንጂ የጠላትየ ጠላት ወዳጄ ነው የሚለው ያረጀ ያፈጀ አውዳሚ ስልት መከተል ለኔ ለአገርና ለህዝብ መቆርቆርን አያሳይም፡፡
እኛ ተቃዋሚዎች ህልማችን ኢህኣዴግን ከስልጣን ለማውረድ ብቻ ሳይሆን ገዚው ፓርቲ ከወረደ በኋላ በአገራችን የተሻለ ሰላም፡ ፍትህ፡ ዲሞክራሲ እና መረጋጋት እንደሚኖርና ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ችግሮችዋ በርግጠኝነት እንደምንፈታላት በተጨባጭ ማረጋገጥ ብሎም ይህንን ከባድ አገራዊ ተልእኮ የሚሸከም ድርጅታዊ መዋቅር መፍጠር ግድ ይለናል፡፡ እስካሁን እንዳየነው የኢህአዴግ አካሄድ በማንኛውም መንገድ እንድታስወግደው እጅግ የሚገፋፋ ነው ሆኖም ግን ከሁሉም በላይ አገር ይቀድማልና አንዳንዴ ለምጣዱ ስንል አይጥዋ እንድትፈነጭ መፍቀድ ሁኔታውን ያስገድደናል፡፡
እስኪ መጀመርያ ድርጅት መመስረት ብቻ ሳይሆን የተመሰረተው ድርጅት በሁሉም ብሄረሰብ ተደማጭ መሆኑንና የሁሉም ህዝብ ፍላጎት ያማከለ ፖሊሲና ስትራተጂ መከተላችን እና ስልጣን ብንይዝ ኢህአዴግ ከስልጣን ወርዶ ኢትዮጵያ እንደማትፈርስ ብቻ ሳይሆን በሁሉም መስኮች የተሻለ ስራ እንደምንሰራ በሳይንሳዊ መንገድ እናረጋግጥ፡፡
እርግጥ ነው የኢህአዴግ መንግስት መቼም ቢሆን ላፀደቀው ህግ ተገዢ እና ታማኝ አይሆንም ፡፡ ነገር ግን ሁሉም ኢትዮጵያውያን የሚመኩበት፡ ውስጠ ዴሞክራሲ ያለው እውነተኛ ህብረ-ብሄር ድርጅት ይኑረንና ምልአተ ህዝቡን ከኋላችን አሰልፈን ማንም ብሄር በሌላው ብሄር ሳይነሳና አንድም ንብረት ሳይወድም በሰላማዊ መንገድ አምባገነኑ መንግስታችን በህዝባዊና ድርጅታዊ ጥንካሬያችን አስጨንቀን ወዶ ሳይሆን ተገዶ ለህግ ተገዢ እንዲሆን ማድረግና የሰከነ ፖለቲካዊ የእርምተ እርምጃዎች በመውስድም ኢህአዴግን ማንበርከክ እንችላለን፡፡ ይህንን ስልጡን ሰላማዊ ስልት ኢህአዴግ ከጦር በላይ እንደሚፈራውና አገራችን ከገባችበት አጣቢቂኝ የሚያወጣ ይመስለኛል፡፡10995826_1561343667457725_6766180167450618065_n

የዞን9 ሴት ተከሳሾች የመብት ጥሰት አቤቱታ! “ፍርድ ቤቱ” ሌላ ቀጠሮ ሰጠ

በቃሊቲ እስር ቤት የሚገኙትን ጦማሪት ማህሌት ፋንታሁን እና ጋዜጠኛ ኤዶም ካሳዬን አያያዝ አስመልክቶ ለዛሬ ተቀጥሮ የነበረው “የፍርድ ቤት” ውሎ የመብት ጥሰቱን አስመልክቶ የማረሚያ ቤቱን ምላሽ በጽሁፍ ለመስማት ነበር ፡፡ ነገር ግን እስር ቤቱ አስተዳደሮች ስብሰባ ላይ በመሆናቸው የጽሁፍ ምላሹ ስላልተፈረመበት ማቅረብ አልቻልንም በማለት የማረሚያ ቤቱ ተወካይ ነኝ ብለው የቀረቡት ዋና ሳጅን ድሪባ ሰበታ ተናግረዋል፡፡

Edom and Mahlet

ዋና ሳጅን ድሪባ የእስር ቤቱ የህግ ባለሞያ እና የሴቶች ክፍል ሰራተኛ ነኝ ፍርድ ቤቱ ከፈቀደ በቃል ምላሽ ልስጥ ያሉ ሲሆን አግባብ ያለው የአስተዳደር ሰው አይደሉም በሚል “ፍርድ ቤቱ” ሳይቀበላቸው ቀርቷል፡፡

በዚህም መሰረት “ፍርድ ቤቱ” የቃሊቲ እስር ቤት አስተዳደር መልሱን በጽሁፍ ይዞ እንዲቀርብ ለየካቲት 25 ቀን 2007 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡( March 4) በተያያዘ ዜና ዓቃቤ ህግ በተከሳሾች ላይ አለኝ ያለውንና ከወንጀል ክሱ ጋር አያይዞ ካቀረበው የማስረጃ ዝርዝር መካከል የሲ.ዲ ማስረጃውን በተመለከተ የተከሳሽ ጠበቆች እስካሁን ስላልደረሳቸው አንዲደርሳቸው በጽሁፍ ጥያቄ አቅርበዋል ፡፡ የጠበቆቸን ጥያቄ ተከትሎ አቃቤ ህግ የሲዲ ማስረጃዎቸቹን ለጠበቆች አንዲያደርስ “ፍርድ ቤቱ” ትዝዛዝ ሰጥቷል፡፡

ደብዳቤ

የዞን9 ማስታወሻ – የሴት እስረኞች መንገላታት በተደጋጋሚ ተገልጾ እና ትእዛዝ ተሰጥቶበት ከመንግሰት በባሰ ጨቋኝ የሆነው “የቃሊቲው መንግሰት” አፈና ያልተሻሻለ አንደሆነ ይታወቃል፡፡ የፓለቲካ እስረኞች አያያዝ የዞን9 ተከሳሾችን ብቻ ሳይሆን ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝን ጋዜጠኛ ርእዬት አለሙን ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋን ጨምሮ የሁሉም ጥያቄ መሆኑ መብት ጥሰቱ በተዘዋዋሪ መንግሰት የሚክደውን ፓለቲካ እስረኛ የለም የሚለውን ሃሳብ በተግባር የሚያረጋግጥ ነው፡፡ ፍርድ ቤቱ ጠንካራ አርምጃ በመውሰድ በሌሎች ጉዳዬች ላይ ያጣውን እምነት አመኔታ እና ስልጣን ቢያንስ የታራሚዎቸን መብት በማስከበር እንዲያሳየው አጥብቀን እንጠይቃለን፡፡ በዚህ የተገለለ የጭቆና አያያዝ ውስጥ ሆነው አንኳን ፈገግታቸው ለአፍታም ያልተገደበው ሴት እስረኛ እህቶቻችን እንደሆነ ከጭቆናው በላይ መሆናቸውን ካስመሰከሩ ቆይተዋል፡፡

አሁንም ስለሚያገባን እንናገራለን
Source: ዞን 9

ሕወሃት እና የባቡር ፖለቲካ – ምላሽ ለሕወሃቱ ጦማሪ – ግርማ ካሳ

10422499_342861759252503_474584120838076462_n“Ethiopia steams ahead with vision for a modern NATIONAL rail network “ ሲሉ ዶ/ር ቴድሮስ ጦምረዋል። እኝህ ሰው ምን ያህል በሶሻል ሜዲያ የሚሰጣቸው አስተያየት እንደሚከታተሉ አላወቅም። ለምን ትንሽ ጊዜ ወስደው ምላሽ ሲሰጡ አላይምና። እርሳቸው አነበቡትም አላነበቡትም፣ ባቡርን በተመለለተ በጫሩት ውይይት ላይ አስተያየት መስጠት እፈልጋለሁ።

በተለያዩ የአገራችን ክፍሎ የባቢር መስመሮችን ለመዘርጋት። ይህ እቅድ በጣም የሚአስይደንቅና የሚያስደስት እቅድ ነው። ሆኖም ማንም የስምንተኛ ክፍል ተማሪ ተመሳሳይ የሚስብ እቅድ በኮምፒተር ዲዛይን ሰርቶ ሊያቀርብ ይችላል። እቅድ ማወጣቱ ላይ አይደለም ትልቁ ቁም ነገር። ነገር ግን እቅዱን መፈጸሙ ላይ ነው።
የዶር ቴድሮስ ሕወሃት ( ሕወሃት የምለው የሚገዛ ሕወሃት በመሆኑ ነው። ሌሎቹ በቁማቸው የሞቱ ናቸዉና) በ2002 ዓ.ም የአምስት አመት እቅድ በሚል፣ በስድስት ኮሪደሮች የባቡር ግንባታ እንደሚያደረግ ተናግሮ ነበር። ይሄን መቼም ዶር ቴዶርስ አይክዱም። በአጠቃላይ በአምስት አመት ዉስጥ ወደ 2300 ኪሎሜትር ለመገንባት ነበር የታቀደው። ኮሮደሮቹም የሚከተሉት ናቸው፡ የአዲስ አበባ መልስተኛ ባቡር፤ የአዲስ አበባ ጅቡቲ ፣ የአዋሽ ወሊዲያ፣ የመቀሌ – ታጁራ፣ የሰበታ- ጂማ-በደሌ፣ የሞጆ-አርባ ምንጭ ወይጦ ኮሮደሮች።

ከነዚህ ዉስጥ ስራ የተጀመረው በሁለቱ ብቻ ነው። የአዲስ አበባ መለስተኛ ባቡር ወደ 34 ኪሎሜትር ብቻ የምትሆን ናት። ሃዲዱ ተዘርግቶ በአንድ መስመር ሙከራ ተደርጓል። ሆኖም በችኮሎ ለምርጫው ሲባል ፣ እቅድና የሕዝቡን ፍላጎት ባካተተ መልኩ ስላልተሰራ፣ ከተማዋን ለሁለት ከፍሏታል። ለሴፍቲ ጥንቃቄ ስላልተደረገም በሃዲዱ መኪናዎች እየሄዱበት ከወዲሁ ጥቅም ላይ ሳይወል እየተበላሸ ነው። ባቡር ለመጀመሪአይ ጊዜ ኢትዮጵያ ዉስጥ የገባ ይመስል (ከመቶ አመት እብፎት አጼ ሚኒሊክ ያስገነቡትን ረስተው) እስክንደነቁር ድረስ ሲለፈፍበት ከቆየው፣ ዶር ቴዶርስን ጨምሮ ፣ የአገዛዙ ባለስልጣናት በሙሉ ታጭቀው ሙከራ ከተደረገበት ቀን ዉጭ፣ ባቡሩ ቆሟል። መቼ ሥራ ላይ እንደሚዉል የሚታወቅ ነገር የለም። የሃዲድ መስመሩ ኤሌትሪክ ሲለቀቅም ብዙዎች ለአደጋ ይጋለጣሉ ተብሎ ይፈራል።

የአዲስ አበባ ጅቡቲ መስመር ምን ያህል እንደተሰራ የሚያወቅ የለም። እዚህ ላይ አንዘንጋ አዲስ መስመር አይደለም የሚሰራው።፡የነበረዉን እንደገና ማደስ ነው። ያለፈው ሰኔ ወር ሪፖርተር ገና እንዳልተጀመረ ነበር የዘገበው። ቢበዛ አሁን ከአዲስ አበባ ሜኤሶ ግማሹ ቢጠናቀቅ ነው። ( ወደ 200 ኪሎሜተር)። ስለዚህ በአጠቃላይ ከ2300 ኪሎሜትር ወደ 300 ብቻ ነው የተሰራው ማለት ነው። በሌሎቹ አራት ኮሪደሮች ግንባታ ገና አልተጀመረም። ከመቀሌ – ታጁራ ላለው መስመር የካቲት 11 በመቀሌ ድንጋይ አኑረዋል።ከጥቂት ቀናት በፊት።

እንግዲህ መጠየቅ ያለብን ለምን ከ2300 ኪሎሜትር 300 ብቻ ሊገነባ ቻለ ? ምንድን ነው ችግሩ ? የሚሉትን ጥያቄዎች ነው። በዋናነት የአመራር ብቃት ማነስ ነው። ሕወሃት የተማሩ ኢንጂነሮችን ሃላፊነት ላይ ማስቀመጥ ሲገባው፣ ወታደር ወርቅነህ ገበየዉን የትራንስፖርት ሚኒስተር አደረጎ ሾመ። ስራዉን ስላልቻለ ይሁን በሌላ ምክንያት ሰዉዬው እንዲለቅ ተደረገ። በምትኩ አቶ መኩሪያ የሚባሉ ሰው ተሾሙ። እርሳቸው ደግሞ በቅርቡ ሙስና ትልቅ ችግር እንደሆነ የገለጸበት ሁኔታ አለ። ከ30 እስከ 40 በመቶ የሚሆን ወጭ በሙስና እንደሚዘረፍ አቶ መኩሪያ እንደተናገሩ ዘገባዎች ይጠቁማሉ።

አንድ ትልቅ ፕሮጀክት ሲሰራ በዋናነት ወጭው መታሰብ አለበት። እንኳን በሌሎች አሥራ አንድ ኮሪደሮች የባቡር መስመሮችን ለመገንባት፣ በዚህ አመት መጠናቀቅ የነበረባቸው ፕሮጀክቶችም የትም አልደረሱም። (እንዳልኩት ከአዲስ አበባ መለስተኛ ባቡር ግንባት ዉጭ) ።

የአዲስ አበባ መለስተኛ ባቡር ወጭ 400 ሚሊዮን ዶላር ነው። ከአዲስ አበባ ጅቡቲ ወደ 2.3 ቢሊዮን ዶላር ሲሆን ከመቀሌ-ወሊድያ (የመቀሌ-ታጁራ ኮሪዶር ግማሹ) 1.5 ቢሊዮን ዶላር ነው። ይሄ ወደ 3.9 ቢሊዮን ዶላር ገንዘብ የሚገኘው በብድር ቻይና ነው። ከአዋሽ – ወልዲያ ላለው መስመር አንድ የስዊስ ባንክ ወደ 1.7 ቢሊዮን ዶላር ያበድራል ተብሎ ይጠበቅ ነበር። ። ብድሩ ግን ምን ደረጃ እንደደረሰ የሚታወቅ ነገር የለም። ለሰበታ-በደሌ እና ሞጆ – ወይጦ ኮሪደሮች እንዲሁም ከወልዲያ -ታጁራ፣ እንኳን ግንባታ ሊጀመር፣ ምንም ብድር እንደሚሰጥም ገና አይታወቅም። የታወቀ ነው ሕወሃት ሁሌ ቅድሚያ ለማን እንደሚሰጥ።

አንደኛ አንድ ትልቅ የኢንጂነሪን ፕሮጀክት እናደርጋለን ከመባሉ በፊት ግንባታዉም በምን ወጭ እንደሚሸፈን መታወቅ አለበት። ሁለተኛ ለግንባታው የሚዉለው ወጭ እንዳይመዘበር ገለልተኛ የሆነ ኦዲተር ያስፈልጋል። ሶስተኛ ለግንባታ የሚዉሉት እቃዎች ጥራት እንዳላቸው ለማረጋገጥ ገለልተኛ የሆነ ኢንጂነርሪን ኢንስፔክተሮች ያስፈልጋሉ። በአጭሩ ግልጽነትና ተጠያቂነት መኖር አለበት። አራተኛ እንደዚህ አይነት ትልቅ ፕሮጀክት ትልቅ ሕዝባዊ ሞቢላይዜሽን ያስፈልጋል። በቻይና ተማምኖ፣ ተተኪ ትዉልድ ያየሌለ ይመስለ ዝም ብሎ መበደር ትልቅ ስህተት ነው። በአገር ቤት ሆነ ቤትውም ከአገር ዉጭ የሚኖረዉም ሕዝብ መረባረብ አለበት። ህዝቡ መታቀፍ አለበት።

አሁን ያለው የሕወሃት መንግስት ፍጹም በሙስና የተጨማለቀ ነው። የተማሩ ኢትዮጵያዉያንን የሚገፋ ነው። እንኳን ሕዝቡን ሊያሰባስብ ህዝቡን እያሸበረ ነው። ከጊዜ ወደ ጊዜ በሕዝቡ እየተጠላ የመጣ ቡድን ነው። ሕወሃቶች ፣ የቻይናዎችን ጫማ እየላሱ የተወሰኑ ነገሮች እያሳዩ፣ በልማት ስም በሕዝብ ስም ከሚገኘው ገንዘን እየሰረቁ ፣ የሚታዩ ጥቂት ግንባታዎችን በሜዲያዎቻቸው ለፖለቲካ ፍጆታ እያሳዩ ያወራሉ እንጂ ኢትዮጵያን በባቡር አያገናኙም። ከምጣዱ ያስታወቅል እኮ ነው የሚባለው። ለ ኤምባሲዎቻቸው የሚከፍሉት እንኳ እስለሌላቸው ለቪዛ የሚጠይቁት እጥፍ አድርገዉታል። ታክሲዎችን በግድ ቦንድ ካልገዛችሁ ብለው ቦሎ አይሰጥጅ እያሏቸው ነው።
ሌላ ምሳሌ ልንገራችሁ። የአባይ ግድብ የት ደረሰ ? ግዱቡ በዚህ አመት ማለቅ ነበረበት። ግን አላለቀም። በዚህ አመት የ ኤሌትሪክ አቅም ወደ 10000 ሜጋ ዋት እናደርሳለን ሲሉ ነበር። ገና 2300 ሜጋ ዋት ናት። ለምን ? የገንዘብ ችግር።

ትዝ ይላቹሃል እንደ አምላክ የሚያመልኩት ሟቹ መለስ ዜናዊ በአስር አመት ዉስጥ ኢትዮጵያዊ ሁሉ በቀን ሶስቴ ይመገባል ያለው። ከጥቂት አመታት በፊርት ቁምስ አሁን ደግሞ ቁምራ የሚባሉ ቃሎች ተፈጥረዋል። ቁምራ ማለት ቁርስ፣ ምሳ ራት አንድ ጊዜ ማለት ነው። የሕወሃት በቀን ሶስት የመመገበ ተስፋ ቁምራን ነው ያተረፈልን።

ሽንፈታዊ አስተሳሰብ ለማራገብ አይደለም።፡ይህ ስርዓት ቢቀየር ወይንም መሰረታዊ የሆኑ ለዉጦች ቢያደረግ፣ ለብሄራዊ እርቅ ቢዘጋጅ፣ ኢትዮጵያዊያንን በዘር መከፋፈሉ ቆሞ ሁሉንም በአንድ ማሰብሰብ ቢቻል፣ እመኑኝ ከቻይናዎች ሳንበደር የታቀደ ግንባታዎች እኛው ራሳችንን መሸፈን እንችላለን። ለምሳሌ ለአዲስ አበባ መለስተኛ ባቡር ግንባታ ወጭው 400 ሚሊዮን ዶላር ነው። ከዚህ 360 ሚሎዮኒ ከቻይና በበድር የተገኘ ነው። በዉጭ አገር የሚኖሩ ኢትዮጵያዉያን ወደ 2 ሚሊዮን ይጠጋሉ። በቀን አንድ ፣ አንድ አንድ ዶላር ቢያዋጡ፣ በስድስት ወር ወጭው ሊሸፈን ይችላል። ይሄን ትልቅ የኢትዮጵያ ሃብት መጠቀም ያልተቻለው ሕወሃት በሚያራምደው ግራዚያናዊ የአፓርታይድ ፖሊሲ ነው።

መልካም አስተዳደር፣ ዲሞክራሲያዊ ስርአት ሕዝብን የሚንቅ፣ የሚከፋፍልና የተጠላ ሳይሆን ሕዝብ የሚያከበር፣ አንድ የሚያደረግና የሚወደድ መንግስት ከመጣ እንኳን የባቡር መስመሮች ሌላም ፣ ሌላም መገንባት እንቻላለን።
በመጨረሻ ለሕወሃቶች ብዙም እንዳይመጻደቅ አንድ ነገር ልበል። ፎቶዎችና ግንባታዎችን የሚያሳዩ ፎቶዎች አትለጥፉልን። ግንብታ የለም አላልንም። ግን ግንባታው እየተሰራ ያለው በቻይናዎች ፣ ከቻይናዎች በተገኘ ብድር ነው። ከቻይና በቻያና ማለት ነው። ስለዚህ አገርችንን የቻይና “ቅኝ ግዛት” በማድረጋችሁ ብዙ አትመጻደቁ። ጣሊያን ኢትዮጵያን ወሮ በነበረ ጊዜም ብዙ የልማት ግንባታዎችን እንደተፈጸሙም አትርሱ።

– See more at: http://satenaw.com/amharic/archives/4923#sthash.IEADwcsm.dpuf