ጋዜጠኛ እና የአዲስ አበባ ባለደራ ምክር ቤት ሰብሳቢ የሆነው እስክንድር ነጋ ትላንት በበርካታ ወጣቶች ተከቦ እንደነበር ለቢቢሲ አረጋግጧል።
“ትናንት ቅዳሜ ምሽት 1፡00 አካባቢ፤ ፒያሳ ጊዮርጊስ ቤተክርስቲያን አካባቢ ከሚገኘው ቢሯችን ስብሰባ ጨርሰን ስንወጣ ነው የተወሰኑ ወጣቶች ናቸው የከበቡን” ይላል እስክንድር።
እስክንድር ቁጥራቸው ከ10 በላይ ይሆናል ያላቸው ሰብሰብ ያሉ ወጣቶች ከቢሮው ውጪ ደጃፍ ላይ ጠብቀው እርሱንና አራት የባልደራስ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባላትን እንደከበቧቸው ያስረዳል።
«አልፈናቸው ስንሄድ በከበባ መልክ ተከትለውናል። እንቅስቃሴያቸው አስጊ ስለነበር ወደ ኋላ ተመልሰን ፖሊስ ይዞ እንዲጠይቅልን ሙከራ አድርገናል። ቢሆንም አንዱ ብቻ ነው በፖሊስ ቁጥጥር ሥራ መዋል የቻለው።»
“የለውጥ አመራሩን ሳይረፍድ ከጥፋት መመለስ ይቻላል” እስክንድር ነጋ
ወጣቶቹ ተቃውሞም ሆነ ጥያቄ አቅርበው ነበር ወይ? ሲጠጓችሁ ዓላማቸው ምንድን ነበር? ተብሎ የተጠየቀው እስክንድር ምንም ያሉን ነገር የለም፤ ነገር ግን በከበባው ውስጥ አስገብተው ተከትለውናል ይላል።
«እኛ ላይ ከሚደርስብን የግድያ ዛቻ አንፃር አስጊ ነበር። እንደዚህ ዓይነት ነገር ተፈጥሮ አያውቅም። ይሄ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው። ብዛት ነበራቸው እና አደጋ ለማድረስ በጣም ቀላል ነበር።»
ወጣቶቹ ጥቃት ሊያደርሱብን ይችሉ ነበር የቦታ መረጣ ጉዳይ እንጂ ብሏል እስክንድር ጨምሮ።
«በእኛ ድምዳሜ ለከበቡን ሰዎች ቦታው አመቺ አልነበረም፤ እኛም ተመለስን። ፊት ለፊታችን ጨለማ ነበር። ከጨለማው ወደኋላ ተመልሰን። እንደ አጋጣሚ አንዲት ፖሊስ ስትመጣ አገኘን። አጠራጣሪ ሁኔታ ስላለ ሰዎቹን እንዲያዙልን እንደምንፈልግ አመለክትን። ተጨማሪ ኃይል ፈልጋ ነበር። በዚያ መሃል ነው እንግዲህ ልጆቹ ተሰባስበው ከአከባቢው የሄዱት።»
ከአንድ ወጣት በቀር የተቀሩት በሚኒባስ እንዳመለጡ የሚናገረው እስክንድር ግለሰቡን ወደ ፖሊስ ጣቢያ ሲወስዱት የፖሊስ አባልና ምክትል ሳጅን ሆኖ ተገኝቷል ይላል።
«ፖሊስ ጣቢያው ቃል ሲሰጥ የደረስንበት ነገር ምክትል ሳጅን መሆኑ ነው። መጀመሪያ ላይ በአካባቢው ምን ሲያደርግ እንደነበር ሲጠየቅ ተማሪ ነኝ ብሎ ነበር። በኋላ ፖሊስ ሆኖ ተገኝቷል። እኛ ቃል ሰጥተን ወደየቤታችን ሄደናል እሱ ፖሊስ ጣቢያ እንዲቆይ ተደርጓል። ዛሬ ጠዋት ተመለሱ ተብለን ስንሄድ ነገ ኑ ተብለናል። ልጁ በእሥር ላይ ይሁን ወይም ለቀውት እንደሆነ የምናውቀው ነገር የለም» ብለል እስክንድር።
ጥበቃ ለእስክንድር. . .?
«በርካታ የግድያ ዛቻ እና ማስፈራሪያ ይደርሰኛል» የሚለው እስክንድር ነጋ ምናልባት ከመንግሥት በኩል ጥበቃ እንዲደረግለት ይፈልግ ይሆን?
«የለም! የለም! እኔ ጥበቃ እንዲደረግልኝም አልፈልግም። የሚያስፈልገው አሁን በተያዘው ልጅ ላይ ጥብቅ የሆነ ምርመራ እንዲደረግ፤ ‘ፌር’ [ፍትሃዊ] የሆነ፤ ሳይንሳዊ የሆነ፤ ሕጉ በሚፈቅደው መሠረት ልጁ እንዲመረመር ነው። በተለይ ከእርሱ ጋር አብረውት የነበሩት ልጆችን አፈላልጎ መያዝና ለምን እንዲህ ዓይነት እንቅስቃሴ እንዳደረጉ መጠየቅ እና ጉዳዩን እስከ ሥር ድረስ ሄዶ መመርመር ነው የሚያስፈልገው። ይሄን ብቻ ነው እኔ ከመንግሥት የምፈልገው።»
እስክንድር ወጣቶቹ ተዘጋጅተውበት እና አጥንተው እንደመጡ ይናገራል። የዕለተ’ለት እንቅሰቃሴያችን ከግምት ውስጥ ገብቷል የሚል ጥርጣሬ እንዳለውም ይናገራል።
«ሁልጊዜ በዚህ ሰዓት ነው የምንጨርሰው። ቅዳሜ ማታ ጨርሰን በእግራችን ነው የምንንቀሳቀሰው። ለምሳሌ እኔ ከጊዮርጊስ ተነስቼ ከአንድ ወይም ከሁለት ሰው ጋር እስከ አራት ኪሎ ደረስ እሄዳለሁ። የተጠና ነው የምለው ለዚህ ነው። ለማናቸውም ዝርዝሩ በፖሊስ የሚረጋገጥ ነገር ነው።»
የተቀናጁ እንቅስቃሴዎች እንዳሉ የአከባቢው ሰው ሲከታተል ነበር የሚለው እስክንድር ዛሬ ጠዋት ምስክሮች ይዘው ወደ ፖሊስ ጣብያ እንደሄዱ ያስረዳል።
«ከእኛ ውጭ የሆኑ፤ በአካባቢው የነበሩ፤ ወጣቶቹ ሲመጡ እና እኛ ላይ ሲያደርጉ የነበረውን የተከታተሉ ሰዎችን ምስክር እንዲሆኑ ይዘን ነው የሄድነው። አስፈላጊ ስለሆነ ማለት ነው። ይሄንን መሠረት አድርጎ ከመንግሥት ትክክለኛ የሆነ ምርመራ አድርጎ እርምጃ እንዲወሰድ ነው። ምክንያቱም ከኃይል እርምጃ ኢትዮጵያ አታተርፍም። በኃይል የሚፈታ የፖለቲካ ጥያቄ የለም።»
እነእስክንድር ምናልባት በቁጥጥር ሥር የዋለው ግለሰብ ቢለቀቅ ክስ የመመሥረት ሃሳብ ይኖራቸው ይሆን?
«እንግዲህ ነገ ነው የምናውቀው። ተለቋል ካሉን ወደ አዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ሄደን የነበረውን ሁኔታ እናስረዳለን። ምስክሮች ይዘን ወደላይ አቤት እንላለን ብለን እናስባለን። በዚያም ደረጃ የማይፈታ ከሆነ ከዚያም ወደላይ ሄደን ማሳሰብ እንፈልጋለን። በመንግሥት ውስጥ ሁለት ሃሳብ አለ ብለን እናስባለን። ብጥብጥ የሚፈልግ ኃይልና ብጥብጥ የማይፈልግ ኃይል አለ። ያንን ግምት ውስጥ በማስገባት እስከ ጥግ ድረስ ሄደን አግባብ ያለው ምርመራ እንዲደረግ ነው የምንፈልገው። ይሄ ልጅ ንፁህ ከሆነ እንዲለቀቅ ነው የምንፈልገው። የግድ መታሠር አለበት የሚል አቋም የለንም።»
ስጋት
እስክንድር፤ ይደርስብኛል ከሚለው ዛቻ እና ማስፈራሪያ አንፃር አደጋ ወይም ጥቃት ይደርስብኛል የሚል ስጋት ይኖርበት ይሆን?
«. . .እኔ የሚጠብቀኝ እግዚአብሔር ነው ብዬ ነው የማስበው። ከዚያ ባሻገር እኔ በግሌ ጥበቃ ይገባኛል ብዬ አላስብም። ጉዳዩ ከእኔ ጋር የተያያዘ አይደለም። የተነሳው ጥያቄ እኔ ኖርኩ አልኖርኩ የሚኖር ነው። በዲሞክራሲያዊ መንገድ እልባት እስካላገኘ ድረስ ማለት ነው። መኖር አልፈልግም ማለት ግን አይደለም» ይላል እስክንድር።
• “ከጄ/ል አሳምነው ጋ በምንም ጉዳይ ያወራሁበት አጋጣሚ የለም” እስክንድር ነጋ
አክሎም «ለሚስቴ መኖር እፈልጋለሁ፤ ለልጄ መኖር እፈልጋለሁ። ኖሬም ደግሞ ለሕብረተሰቡ ገንቢ የሆነ አስተዋፅዖ ማድረግ እፈልጋለሁ። ጥበቃ ግን ይከብደኛል። ኅሊናዬም አይፈቅደውም። ካለው ዛቻ አኳያ፤ በተለይ ደግሞ ትላንት በተግባር ስላየነው አያሳስበኝም ማለት ግን አልችልም፤ ያሳስበኛል» ብሏል።
ቢቢሲ ጉዳዩን በተመለከተ ፖሊስ በኩል ያለውን አስተያየት ለማወቅ ያደረገው ጥረት ሳይሳካ ቀርቷል።
– #BBC