በትግራይ ክልል በዳንሻ፣ወልቃይት ጠገዴ አካባቢዎች የሚገኙ በአማራ የወልቃይት ህዝቦች ላይ ዘርን መሰረት ያደረገ ጥቃት እንደተፈፀመባቸው ተፈናቃዮች ተናገሩ

(North Gondar communication)

ቁጥራቸው ከ80 በላይ የሆኑ የአማራ ወልቃይት ህዝቦች በአማረኛ ቋንቋ ለምን ትናገራላችሁ በሚል ሰበብ በትግራይ ልዩ ሀይል ፖሊስ ድብደባና ግድያ እንደተፈፀባቸው ይናገራሉ፡፡ 
ተፈናቃዮቹ ከደረሰባቸው ችግር ለማምለጥ ለ4 ተከታታይ ቀናት ከአስቸጋሪ የእግር ጉዞ በኋላ በአማራ ክልል ሶሮቃ ከተማ መግባት ችለዋል፡፡
ተፈናቃዮች እንደሚሉት የወልቃይት ጠገዴ ህዝብ አማራ ማንነቱን በመጠየቁ ምክንያት በህወሃት አመራሮች ትዕዛዝ በክልሉ ልዩ ሀይል ፖሊስ ከፍተኛ ድብደባና ግድያ እየተፈፀመብን ነው ብለዋል፡፡
የህወሃት አመራሮች እናንተ አማራዎች ሳትሆኑ ከተንቤየን የመጣችሁ ትግሬዎች ናችሁ በማለት በማነነታችን ላይ ከፍተኛ የስነ ልቦናና የአካል ጉዳት እያደረሱብን በመሆኑ የፌደራል መንግስት የመከላከያ ሰራዊትና የፌደራል ፖሊስ በአካባቢው እንዲያሰማራ ጠይቀዋል፡፡
ተማሪ ዳንቸል ገብረ መድህን እና ተማሪ አስፋው ክንፉ የአራተኛ እና የአምስተኛ ክፍል ተማሪዎች ናቸው፡፡ ተማሪዎቹ እንደሚሉት በምንማርበት ክፍል ውስጥ አማርኛ ቋንቋን ተናግራችኋል ተብለን ከአደግንበት እና ከተማርነበት አካባቢ እንድንፈናቀል ተገደናል በማለት ይናገራሉ፡፡
በተለይም ወጣቶቹ እንደሚናገሩት ትምህርት ስንማር በአማረኛ ቋንቋ ሳይሆን በትግረኛ ቋንቋ ብቻ ተገደን እንድንማር በመገደዳችን በትምህርት ውጤታችን ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ እያሳደረብን ነው ብለዋል፡፡
ተፈናቃዮቹ አያይዘውም አማራ በመሆናችን ብቻ በኢኮኖሚና በማህበራዊ ኑሮአችን ላይ ችግሮች ከመፈጠሩ በተጨማሪ ተመልሰን ወደ አካባቢያችን ብንሄድ በህወሃት አመራሮችና በክልሉ የፖሊስ ልዩ ሀይል ከመታሰር፣ ከመደብደብና ከመገደል አናመልጥም በመሆኑም መንግስት ዘላቂ መፍትሄ ሊያበጅልን ይገባል ሲሉ ተፈናቃዮች ጠይቀዋል፡፡
ከትግራይ ክልል የተፈናቀሉት የአማራ የወልቃይት ህዝቦች አክለው እንደተናገሩት የህወሃት ባለስልጣናት የወልቃይት ሙሁራንና ታላላቅ አባቶችን በማሰርና በመግደል አካባቢውን በትግሬ ህዝብ ለመተካት ያላሠለሠ ጥረት በማድረግ ላይ ይገኛሉ፡፡

የወልቃይት የአማራ አስመላሽ ኮሚቴ ምክትል ሊቀመንበር የሆኑት አቶ አታላይ ዛፌ እንደተናገሩት የአማራ ማንነታቸውንና ባህላቸውን በማንፀባረቃቸው የተለያዩ የሰብዓዊና የመብት ጥሰቶች እየተካሄደባቸው በመሆኑ በርካታ ሰዎች ተፈናቅለው በበርሃና በእስራት ውስጥ እንደሚገኙ አንስተዋል፡፡

በመሆኑም መንግስት በነዋሪዎች ላይ እየደረሰ ያለውን ችግርና እንግልት ተገንዝቦ በቦታው ላይ የሀገር መከላከያ ሰራዊት በማስገባት የነዋሪዎችን ሰላም ሊያስጠብቅ ይገባል ብለዋል፡፡
አቶ አታላይ ዛፌ አክለውም የወልቃይት የአማራ ማንነት ጉዳይ ህገ መንግስቱን መሠረት ያላደረገና የህወሃትን ፍላጎት ብቻ ትኩረት ያደረገ በመሆኑ በዘላቂነት ከህግ አንፃር መንግስት ችግሩን በአፋጣኝ እንዲፈታ ጠይቀዋል፡፡

በመጨረሻም አሁን ባለው ሁኔታ ለተፈናቃይ ወገኖች የሶሮቃ ከተማ እና በአካባቢው የሚኖሩ ህዝቦች የተለያዩ ድጋፎችን እያደረጉላቸው ይገኛል፡፡
መስራት መኖር ማርጀት መሞት በሀገር ነው፡፡በራሳችን ሀገር ተፈናቃይ እና ስደተኛ መሆን የለብንም፡፡በአማራነታችን እንኮራበታለን እንጅ አናፍርበትም መብታችን ሊከበርልን ይገባል፡፡ ተፈናቃዮች ካሰሟቸው መልዕክቶች በጥቂቱ የተወሰዱ ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡

Leave a comment